ምዕራፍ 5።

1፤ ተመልሼም ዓይኖቼን አነሣሁ፥ እነሆም፥ አንድ በራሪ የመጽሐፍ ጥቅልል አየሁ።

2፤ እርሱም። የምታየው ምንድር ነው? አለኝ። እኔም። በራሪ የመጽሐፍ ጥቅልል አያለሁ፤ ርዝመቱ ሀያ ክንድ ወርዱም አሥር ክንድ ነው አልሁ።

3፤ እንዲህም አለኝ። ይህ በምድር ፊት ሁሉ ላይ የሚወጣው እርግማን ነው፤ የሚሰርቅ ሁሉ በእርሱ ላይ በዚህ በኩል እንደ ተጻፈው ሁሉ ይጠፋል፥ በሐሰት የሚምልም ሁሉ በእርሱ ላይ በዚያ በኩል እንደ ተጻፈው ሁሉ ይጠፋል።

4፤ እኔ አስወጣዋለሁ፥ ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፥ ወደ ሚሰርቀውም ቤት፥ በሐሰትም በስሜ ወደሚምለው ቤት ይገባል፤ በቤቱም ውስጥ ይኖራል፥ እርሱንም፥ እንጨቱንና ድንጋዩን፥ ይበላል።

5፤ ከእኔም ጋር ይነጋገር የነበረው መልአክ ወጥቶ። ዓይኖችህን አንሣ፥ ይህችም የምትወጣው ምን እንደ ሆነች እይ አለኝ።

6፤ እኔም። ምንድር ናት? አልሁ። እርሱም። ይህች የምትወጣው የኢፍ መስፈሪያ ናት አለኝ። ደግሞም። በምድር ሁሉ ላይ ያለ በደላቸው ይህ ነው አለ።

7፤ እነሆም፥ የእርሳሱን መክሊት አነሡት፤ እነሆም፥ በኢፍ መስፈሪያው ውስጥ አንዲት ሴት ተቀምጣ ነበር።

8፤ እርሱም። ይህች ክፋት ናት አለኝ፤ በኢፍ መስፈሪያው ውስጥ ጣላት፥ የእርሳሱንም ጠገራ በመስፈሪያ አፍ ላይ ጣለ።

9፤ ዓይኖቼንም አንሥቼ አየሁ፥ እነሆም፥ ሁለት ሴቶች ወጡ፥ ነፋስም በክንፎቻቸው ነበረ፤ ክንፎቻቸውም እንደ ሽመላ ክንፎች ነበሩ፤ የኢፍ መስፈሪያውንም በምድርና በሰማይ መካከል አነሡት።

10፤ ከእኔም ጋር ይነጋገር የነበረውን መልአክ። እነዚህ የኢፍ መስፈሪያውን ወዴት ይወስዱታል? አልሁት።

11፤ እርሱም። በሰናዖር ምድር ቤት ይሠሩለት ዘንድ ይወስዱታል፤ በተዘጋጀም ጊዜ በዚያ በስፍራው ይኖራል አለኝ።