መዝሙር 61

ለመዘምራን አለቃ፤ በበገናዎች፤ የዳዊት መዝሙር።

1 አምላክ ሆይ፥ ልመናዬን ስማ፥ ጸሎቴንም አድምጥ።

2 ልቤ ተስፋ በቈረጠ ጊዜ ከምድር ዳርቻ ወደ አንተ እጮኻለሁ፤ በድንጋይ ላይ ከፍ ከፍ አደረግኸኝ።

3 ጽኑ ግንብ በጠላት ፊት ተስፋዬም ሆነኸኛልና መራኸኝ።

4 በድንኳንህ ለዘላለም እኖራለሁ፤ በክንፎችህም ጥላ እጋረዳለሁ፤

5 አቤቱ፥ አንተ ስእለቴን ሰምተሃልና፤ ስምህንም ለሚፈሩ ርስትህን ሰጠሃቸው።

6 ለንጉሥ ከቀን በላይ ቀን ትጨምራለህ፥ ዓመታቱም ከትውልድ ወደ ትውልድ ይሆናሉ።

7 በእግዚአብሔር ፊት ለዘላለም ይኖራል፤ ይጠብቁት ዘንድ ምሕረትንና እውነትን አዘጋጅለት።

8 እንዲሁ ለስምህ ለዘላለም እዘምራለሁ ስእለቴን ሁልጊዜ እፈጽም ዘንድ።