መዝሙር 25

የዳዊት መዝሙር።

1 አቤቱ፥ ወደ አንተ ነፍሴን አነሣለሁ።

2 አምላኬ፥ አንተን ታመንሁ፤ አልፈር፥ ጠላቶቼ በእኔ አይሣቁብኝ።

3 አንተን ተስፋ የሚያደርጉ አያፍሩም፤ በከንቱ የሚገበዙ ያፍራሉ።

4 አቤቱ፥ መንገድህን አመልክተኝ፥ ፍለጋህንም አስተምረኝ።

5 አንተ የመድኃኒቴ አምላክ ነህና በእውነትህ ምራኝ፥ አስተምረኝም፤ ቀኑን ሁሉ አንተን ተስፋ አድርጌአለሁ።

6 አቤቱ፥ ምሕረትህንና ቸርነትህን አስብ፥ ከጥንት ጀምሮ ናቸውና።

7 የልጅነቴን ኃጢአትና መተላለፍ አታስብብኝ፤ አቤቱ፥ ስለ ቸርነትህ ብዛት እንደ ምሕረትህ አስበኝ።

8 እግዚአብሔር ቸር ቅንም ነው፤ ስለዚህ ኃጢአተኞችን በመንገድ ይመራቸዋል።

9 ገሮችን በፍርድ ይመራል፥ ለገሮችም መንገድን ያስተምራቸዋል።

10 የእግዚአብሔር መንገድ ሁሉ ቸርነትና እውነት ነው። ቃል ኪዳኑንና ምስክሩን ለሚጠብቁ።

11 አቤቱ፥ ኃጢአቴ እጅግ ነውና ስለ ስምህ ይቅር በለኝ።

12 እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው ማን ነው? በሚመርጠው መንገድ ያስተምረዋል።

13 ነፍሱ በመልካም ታድራለች፥ ዘሩም ምድርን ይወርሳል።

14 እግዚአብሔር ለሚፈሩት ኃይላቸው ነው፥ ቃል ኪዳኑንም ያስታውቃቸዋል።

15 እርሱ እግሮቼን ከወጥመድ ያወጣቸዋልና ዓይኖቼ ሁልጊዜ ወደ እግዚአብሔር ናቸው።

16 እኔ ብቻዬንና ችግረኛ ነኝና ፊትህን ወደ እኔ አድርግ ማረኝም።

17 የልቤ ችግር ብዙ ነው፤ ከጭንቀቴ አውጣኝ።

18 ድካሜንና መከራዬን እይ፥ ኃጢአቴንም ሁሉ ይቅር በለኝ።

19 ጠላቶቼ እንደ በዙ እይ፥ የግፍም ጥል ጠልተውኛል።

20 ነፍሴን ጠብቅና አድነኝ፤ አንተን ታምኛለሁና አልፈር።

21 አንተን ተስፋ አድርጌአለሁና የውሃትና ቅንነት ይጠብቁኝ።

22 አቤቱ፥ እስራኤልን ከመከራው ሁሉ አድነው።