መዝሙር 20

ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።

1 በመከራ ቀን እግዚአብሔር ይስማህ፤ የያዕቆብ አምላክ ስም ያቁምህ።

2 ከመቅደሱ ረድኤትን ይላክልህ፥ ከጽዮንም ያጥናህ።

3 ቍርባንህን ሁሉ ያስብልህ፤ የሚቃጠል መሥዋዕትህን ያለምልምልህ።

4 እንደ ልብህ ይስጥህ ፈቃድህንም ሁሉ ይፈጽምልህ።

5 በማዳንህ ደስ ይለናል፤ በአምላካችን ስም ከፍ ከፍ እንላለን፤ ልመናህን ሁሉ እግዚአብሔር ይፈጽምልህ።

6 እግዚአብሔር የቀባውን እንዳዳነው ዛሬ አወቅሁ፤ ከሰማይ መቅደሱ ይመልስለታል፤ በቀኙ ብርታት ማዳን።

7 እነዚያ በሰረገላ እነዚያም በፈረስ ይታመናሉ፤ እኛ ግን በአምላካችን በእግዚአብሔር ስም ከፍ ከፍ እንላለን።

8 እነርሱ ተሰነካክለው ወደቁ፤ እኛ ግን ተነሣን፥ ጸንተንም ቆምን።

9 አቤቱ፥ ንጉሥን አድነው፥ በጠራንህም ቀን ስማን።