መዝሙር 16

የዳዊት ቅኔ።

1 አቤቱ፥ በአንተ ታምኛለሁና ጠብቀኝ።

2 እግዚአብሔርን። አንተ ጌታዬ ነህ አልሁ፤ ከአንተ በቀር በጎነት የለኝም።

3 ፈቃድህ ሁሉ በምድር ባሉት ቅዱሳንና ክቡራን ላይ ነው።

4 ወደ ሌላ ለሚፋጠኑት መከራቸው ይበዛል፤ የቍርባናቸውን ደም እኔ አላፈስሰውም፥ ስማቸውንም በከንፈሬ አልጠራም።

5 እግዚአብሔር የርስቴ እድል ፈንታና ጽዋዬ ነው፥ ዕጣዬንም የምታጠና አንተ ነህ።

6 ገመድ ባማረ ስፍራ ወደቀችልኝ፥ ርስቴም ተዋበችልኝ።

7 የመከረኝን እግዚአብሔርን እባርካለሁ፤ ደግሞም በሌሊት ኵላሊቶቼ ይገሥጹኛል።

8 ሁልጊዜ እግዚአብሔርን በፊቴ አየዋለሁ፤ በቀኜ ነውና አልታወክም።

9 ስለዚህ ልቤን ደስ አለው ምላሴም ሐሴት አደረገች፤ ሥጋዬም ደግሞ በተስፋ ታድራለች፤

10 ነፍሴን በሲኦል አትተዋትምና፥ ቅዱስህንም መበስበስን ያይ ዘንድ አትተወውም።

11 የሕይወትን መንገድ አሳየኸኝ፤ ከፊትህ ጋር ደስታን አጠገብኸኝ፥ በቀኝህም የዘላለም ፍሥሐ አለ።