መዝሙር 149

1 ሃሌ ሉያ። ለእግዚአብሔር አዲሱን ቅኔ ተቀኙለት፤ ምስጋናው በቅዱሳኑ ጉባኤ ነው።

2 እስራኤል በፈጣሪው ደስ ይበለው፥ የጽዮንም ልጆች በንጉሣቸው ሐሤትን ያድርጉ።

3 ስሙን በዘፈን ያመስግኑ፥ በከበሮና በመሰንቆም ይዘምሩለት።

4 እግዚአብሔር በሕዝቡ ተደስቶአልና፥ የዋሃንንም በማዳኑ ከፍ ከፍ ያደርጋልና።

5 ቅዱሳን በክብር ይመካሉ፤ በምንጣፋቸውም ላይ ሐሤትን ያደርጋሉ።

6 የእግዚአብሔር ምስጋና በጕሮሮአቸው ነው፤ ሁለት አፍ ያለውም ሰይፍ በእጃቸው ነው፥

7 በአሕዛብ ላይ በቀልን በሰዎችም መካከል ቅጣትን ያደርጉ ዘንድ፤

8 ንጉሦቻቸውን በሰንሰለት፥ አለቆቻቸውንም በእግር ብረት ያስሩ ዘንድ፤

9 የተጻፈውን ፍርድ ያደርጉባቸው ዘንድ። ለቅዱሳን ሁሉ ይህች ክብር ናት። ሃሌ ሉያ።