መዝሙር 148

የሐጌና የዘካርያስ መዝሙር።

1 ሃሌ ሉያ። እግዚአብሔርን ከሰማያት አመስግኑት፤ በአርያም አመስግኑት።

2 መላእክቱ ሁሉ፥ አመስግኑት፤ ሠራዊቱ ሁሉ፥ አመስግኑት።

3 ፀሐይና ጨረቃ፥ አመስግኑት፤ ከዋክብትና ብርሃን ሁሉ፥ አመስግኑት።

4 ሰማየ ሰማያት፥ አመስግኑት የሰማያት በላይም ውኃ።

5 እርሱ ብሎአልና፥ ሆኑም፤ እርሱም አዝዞአልና፥ ተፈጠሩም፤ የእግዚአብሔርን ስም ያመስግኑት።

6 ለዘላለም ዓለም አቆማቸው፤ ትእዛዝን ሰጠ፥ አያልፉምም።

7 እባቦች ጥልቆችም ሁሉ፥ እግዚአብሔርን ከምድር አመስግኑት፤

8 እሳትና በረዶ አመዳይና ውርጭ፥ ቃሉን የሚያደርግ ዐውሎ ነፋስም፤

9 ተራሮች ኰረብቶችም ሁሉ፥ የሚያፈራም ዛፍ ዝግባም ሁሉ፤

10 አራዊትም እንስሳትም ሁሉ፥ ተንቀሳቃሾችም የሚበርሩ ወፎችም፤

11 የምድር ነገሥታት አሕዛብም ሁሉ፥ አለቆች የምድርም ፈራጆች ሁሉ፥

12 ጕልማሶችና ቈነጃጅቶች፥ ሽማግሌዎችና ልጆች፤

13 የእግዚአብሔርን ስም ያመስግኑ፤ ስሙ ብቻውን ከፍ ከፍ ብሎአልና፥ ምስጋናውም በሰማይና በምድር ላይ ነው።

14 የሕዝቡንም ቀንድ ከፍ ከፍ ያደርጋል፤ የቅዱሳኑንም ሁሉ ምስጋና ወደ እርሱ ለቀረበ ለእስራኤል ልጆች ሕዝብ ከፍ ከፍ ያደርጋል። ሃሌ ሉያ።