መዝሙር 13

ለመዘምራን አለቃ፤ የዳዊት መዝሙር።

1 አቤቱ፥ እስከ መቼ ፈጽመህ ትረሳኛለህ? እስከ መቼስ ፊትህን ከእኔ ትሰውራለህ?

2 እስከ መቼ በነፍሴ እመካከራለሁ? ትካዜስ እስከ መቼ ሁልጊዜ ይሆናል? እስከ መቼ ጠላቴ በላዬ ይጓደዳል?

3 አቤቱ አምላኬ፥ እየኝ ስማኝም፤ ጠላቴ። አሸነፍሁት እንዳይል፥

4 የሚያስጨንቁኝም እኔ ብናወጥ ደስ እንዳይላቸው፥ ለሞትም እንዳልተኛ ዓይኖቼን አብራ።

5 እኔ ግን በቸርነትህ ታመንሁ፥ ልቤም በመድኃኒትህ ደስ ይለዋል።

6 የረዳኝን እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ፥ ለልዑል እግዚአብሔር ስምም እዘምራለሁ።