መዝሙር 129

የመዓርግ መዝሙር።

1 እስራኤል። ከትንሽነቴ ጀምሮ ብዙ ጊዜ ተሰለፉብኝ ይበል፤

2 ከትንሽነቴ ጀምሮ ብዙ ጊዜ ተሰለፉብኝ፤ ነገር ግን አላሸነፉኝም።

3 ኃጢአተኞች በጀርባዬ ላይ መቱኝ፥ ኃጢአታቸውንም አስረዘሙአት።

4 እግዚአብሔር ጻድቅ ነው፤ የኃጢአተኞችን አንገታቸውን ቈረጠ።

5 ጽዮንን የሚጠሉ ሁሉ ይፈሩ፥ ወደ ኋላቸውም ይመለሱ።

6 በሰገነት ላይ እንደ በቀለ ሣር፥ ሳይነቀል እንደሚደርቅ፥

7 ለሚያጭደው እጁን፥ ነዶዎቹን ለሚሰበስብ እቅፉን እንደማይሞላ ይሁኑ።

8 በመንገዱም የሚያልፉ። የእግዚአብሔር በረከት በእናንተ ላይ ይሁን፤ በእግዚአብሔር ስም እንመርቃችኋለን አይሉም።