መዝሙር 125

የመዓርግ መዝሙር።

1 በእግዚአብሔር የታመኑ እንደማይታወክ ለዘላለም እንደሚኖር እንደ ጽዮን ተራራ ናቸው።

2 ተራሮች በኢየሩሳሌም ዙሪያ እንደ ሆኑ፥ ከዛሬ ጀምሮ ለዘላለም፤ እግዚአብሔር በሕዝቡ ዙሪያ ነው።

3 ጻድቃን እጃቸውን ወደ ክፋት እንዳይዘረጉ የኃጥኣን በትር በጻድቃን ዕጣ ላይ አይኖርም።

4 አቤቱ፥ ለቸሮች ልባቸውም ለቀና መልካምን አድርግ።

5 ወደ ጠማማነት የሚመለሱትን ግን ዓመፃን ከሚሠሩት ጋር እግዚአብሔር ይወስዳቸዋል። ሰላም በእስራኤል ላይ ይሁን።