መዝሙር 122

የዳዊት የመዓርግ መዝሙር።

1 ወደ እግዚአብሔር ቤት እንሄድ ባሉኝ ጊዜ ደስ አለኝ።

2 ኢየሩሳሌም ሆይ፥ እግሮቻችን በአደባባይሽ ቆሙ።

3 ኢየሩሳሌምስ እርስ በርስዋ እንደ ተገጠገጠች ከተማ ተሠርታለች።

4 የእግዚአብሔርን ስም ያመስግኑ ዘንድ፥ ለእስራኤል ምስክር ሊሆኑ የእግዚአብሔር ነገዶች ወደዚያ ይወጣሉ።

5 ዙፋኖች በዚያ ለፍርድ ተቀምጠዋልና፥ የዳዊት ቤት ዙፋኖች።

6 ለኢየሩሳሌም ሰላምን ለምኑ፤ አንተንም ለሚወድዱ ልማት ይሁን።

7 በኃይልህ ሰላም፥ በጌጠኛ ቤትህም ልማት ይሁን።

8 ስለ ወንድሞቼ ስለ ባልንጀሮቼም፥ በውስጥሽ ሰላም ይሁን አልሁ።

9 ስለ አምላካችን ስለ እግዚአብሔር ቤት ላንቺ መልካምነትሽን ፈለግሁ።