መዝሙር 101

የዳዊት መዝሙር።

1 አቤቱ፥ ምሕረትንና ፍርድን እቀኝልሃለሁ።

2 እዘምራለሁ፥ ንጹሕ መንገዱንም አስተውላለሁ፤ ወደ እኔ መቼ ትመጣለህ? በቤቴ መካከል በልቤ ቅንነት እሄዳለሁ።

3 በዓይኔ ፊት ክፉን ነገር አላኖርሁም፤ ሕግ ተላላፊዎችን ጠላሁ።

4 ጠማማ ልብም አልተጠጋኝም፤ ክፉ ከእኔ በራቀ ጊዜ አላወቅሁም።

5 ባልንጀራውን በቀስታ የሚያማን እርሱን አሳደድሁ፤ በዓይኑ ትዕቢተኛ የሆነውና ልቡ የሚሳሳው ከእኔ ጋር አይተባበርም።

6 ከእኔ ጋር ይኖሩ ዘንድ፤ ዓይኖቼ በምድር ምእመናን ላይ ናቸው፤ በቀና መንገድ የሚሄድ እርሱ ያገለግለኛል።

7 ትዕቢትን የሚያደርግ በቤቴ መካከል አይኖርም፤ ዓመፅን የሚናገር በዓይኔ ፊት አይቀናም።

8 ዓመፃ የሚያደርጉትን ሁሉ ከእግዚአብሔር ከተማ አጠፋቸው ዘንድ፥ የምድርን ኃጢአተኞች ሁሉ በማለዳ እገድላቸዋለሁ።