መዝሙር 3

ከልጁ ከአቤሴሎም ፊት በሸሸ ጊዜ የዳዊት መዝሙር።

1 አቤቱ፥ የሚያስጨንቁኝ ምንኛ በዙ! በኔ ላይ የሚቆሙት ብዙ ናቸው።

2 ብዙ ሰዎች ነፍሴን። አምላክሽ አያድንሽም አልዋት።

3 አንተ ግን አቤቱ፥ መጠጊያዬ ነህ፥ ክብሬንና ራሴንም ከፍ ከፍ የምታደርገው አንተ ነህ።

4 በቃሌ ወደ እግዚአብሔር እጮሃለሁ ከተቀደሰ ተራራውም ይሰማኛል።

5 እኔ ተኛሁ አንቀላፋሁም፤ እግዚአብሔርም ደግፎኛልና ነቃሁ።

6 ከሚከብቡኝ ከአእላፍ ሕዝብ አልፈራም።

7 ተነሥ፥ አቤቱ፤ አምላኬ ሆይ፥ አድነኝ፤ አንተ የጠላቶቼን መንጋጋ መትተሃልና፥ የክፉዎችንም ጥርስ ሰብረሃልና።

8 ማዳን የእግዚአብሔር ነው፥ በረከትህም በሕዝብህ ላይ ነው።