ምዕራፍ 21

1 የንጉሥ ልብ እንደ ውኃ ፈሳሾች በእግዚአብሔር እጅ ነው፤ ወደ ወደደውም ያዘነብለዋል።

2 የሰው መንገድ ሁሉ በዓይኑ ፊት የቀናች ትመስለዋለች፤ እግዚአብሔር ግን ልብን ይመዝናል።

3 እግዚአብሔር ከመሥዋዕት ይልቅ ጽድቅንና ቅን ነገርን ማድረግ ይወድዳል።

4 ትዕቢተኛ ዓይንና ደፋር ልብ የኀጥኣንም እርሻ ኃጢአት ነው።

5 የትጉህ አሳብ ወደ ጥጋብ ያደርሳል፤ ችኵል ሰው ሁሉ ግን ለመጕደል ይቸኩላል።

6 በሐሰተኛ ምላስ መዝገብ ማከማቸት የሚበንን ጉም ነው፤ ይህን የሚፈልጉ ሞትን ይፈልጋሉ።

7 ቅን ነገርን ያደርጉ ዘንድ አይወድዱምና የኀጥኣን ንጥቂያ ራሳቸውን ያጠፋቸዋል።

8 የበደለኛ መንገድ የጠመመች ናት፤ የንጹሕ ሥራ ግን የቀና ነው።

9 ከጠበኛ ሴት ጋር በአንድ ቤት ከመቀመጥ በውጪ በቤት ማዕዘን ላይ መቀመጥ ይሻላል።

10 የኀጥእ ነፍስ ክፉን ትመኛለች፥ በፊቱም ባልንጀራው ሞገስን አያገኝም።

11 ፌዘኛ ቅጣትን በተቀበለ ጊዜ አላዋቂ ሰው ጥበብን ያገኛል፤ ጠቢብም ቢማር እውቀትን ይቀበላል።

12 ጻድቅ ስለ ኀጥእ ቤት ያስባል፥ ኀጥኣንም ለጥፋት እንደ ተገለበጡ።

13 የድሀውን ጩኸት እንዳይሰማ ጆሮውን የሚደፍን ሰው፥ እርሱ ራሱ ይጮኻል አይሰማለትምም።

14 ስጦታ በስውር ቍጣን ታጠፋለች፥ የብብትም ውስጥ ጉቦ ጽኑ ቍጣን ታበርዳለች።

15 ፍርድን ማድረግ ለጻድቅ ደስታ ነው፤ ኃጢአትን ለሚያደርጉ ግን ጥፋት ነው።

16 ከማስተዋል መንገድ የሚሳሳት ሰው በሙታን ጉባኤ ያርፋል።

17 ተድላ የሚወድድ ድሀ ይሆናል፥ የወይን ጠጅንና ዘይትንም የሚወድድ ባለጠጋ አይሆንም።

18 ኀጥእ የጻድቅ ቤዛ ነው፤ በደለኛም የቅን ሰው ቤዛ ነው።

19 ከጠበኛና ከቍጡ ሴት ጋር ከመቀመጥ በምድረ በዳ መቀመጥ ይሻላል።

20 የከበረ መዝገብና ዘይት በጠቢብ ሰው ቤት ይኖራል። አእምሮ የሌለው ሰው ግን ይውጠዋል።

21 ጽድቅንና ምሕረትን የሚከተል ሕይወትንና ጽድቅን ክብርንም ያገኛል።

22 ጠቢብ የኃያላንን ከተማ ይገባባታል፥ የሚታመኑበትንም ኃይል ያፈርሳል።

23 አፉንና ምላሱን የሚጠብቅ ነፍሱን ከመከራ ይጠብቃል።

24 ኵሩና ተጓዳጅ ሰው ፌዘኛ ይባላል፤ እርሱም በትዕቢት ቍጣ ያደርጋል።

25 ታካችን ምኞቱ ትገድለዋለች፥ እጆቹ ይሠሩ ዘንድ አይፈቅዱምና።

26 ኀጥእ ቀኑን ሁሉ ምኞትን ይመኛል፤ ጻድቅ ግን ይሰጣል፥ አይሰስትም።

27 የኀጥኣን መሥዋዕት አስጸያፊ ነው፤ ይልቁንም በክፉ አሳብ ሲያቀርቡት አስጸያፊ ነው።

28 ሐሰተኛ ምስክር ይጠፋል፤ የሚሰማ ሰው ግን ተጠንቅቆ ይናገራል።

29 ኀጥእ ፊቱን ያጠነክራል፤ ቅን ሰው ግን መንገዱን ያጸናል።

30 ጥበብ ወይም ማስተዋል ወይም ምክር በእግዚአብሔር ላይ የለም።

31 ፈረስ ለጦርነት ቀን ይዘጋጃል፤ ድል ግን ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው።