ምዕራፍ 20

1 የወይን ጠጅ ፌዘኛ ያደርጋል፥ ብርቱ መጠጥም ጠበኛ ያደርጋል፤ በዚህም የሳተ ሁሉ ጠቢብ አይደለም።

2 የንጉሥ ቍጣ እንደ አንበሳ ግሣት ነው፤ የሚያስቈጣውም ሰው የራሱን ነፍስ ይበድላል።

3 ከክርክር ይርቅ ዘንድ ለሰው ክብሩ ነው፤ ሰነፍ ሁሉ ግን እንዲህ ባለ ነገር ይጣመራል።

4 ታካች ሰው በብርድ ምክንያት አያርስም፤ ስለዚህ በመከር ይለምናል፥ ምንም አያገኝም።

5 ምክር በሰው ልብ እንደ ጠሊቅ ውኃ ነው፤ አእምሮ ያለው ሰው ግን ይቀዳዋል።

6 ብዙ ሰዎች ቸርነታቸውን ያወራሉ፤ የታመነውን ሰው ግን ማን ያገኘዋል?

7 ጻድቅ ያለ ነውር ይሄዳል፥ ልጆቹም ከእርሱ በኋላ ምስጉኖች ናቸው።

8 በፍርድ ወንበር የተቀመጠ ንጉሥ ክፉውን ሁሉ በዓይኖቹ ይበትናል።

9 ልቤን አነጻሁ፥ ከኃጢአትም ጠራሁ የሚል ማን ነው?

10 ሁለት ዓይነት ሚዛንና ሁለት ዓይነት መስፈሪያ፥ ሁለቱ በእግዚአብሔር ፊት ርኩሳን ናቸው።

11 ሕፃን ቅንና ንጹሕ መሆኑ በሚያደርገው ሥራ ይታወቃል።

12 የሚሰማ ጆሮንና የሚያይ ዓይንን፥ ሁለቱን እግዚአብሔር ፈጠራቸው።

13 ድሀ እንዳትሆን እንቅልፍን አትውደድ፤ ዓይንህን ክፈት፥ እንጀራም ትጠግባለህ።

14 የሚገዛ ሰው። ክፉ ነው ክፉ ነው ይላል፤ በሄደ ጊዜ ግን ይመካል።

15 ወርቅና ብዙ ቀይ ዕንቍ ይገኛል፤ የእውቀት ከንፈር ግን የከበረች ጌጥ ናት።

16 ለማያውቀው ከተዋሰ ሰው ልብሱን ውሰድ፥ ለእንግዳ የተዋሰውንም እርሱን አግተው።

17 የሐሰት እንጀራ ለሰው የጣፈጠ ነው፤ ከዚያ በኋላ ግን አፉ ጭንጫ ይሞላል።

18 አሳብ በምክር ትጸናለች፥ በመልካምም ምክር ሰልፍ አድርግ።

19 ዘዋሪ ሐሜተኛ ምሥጢርን ይገልጣል፤ ከንፈሩን የሚያሞጠሙጥ ሰውን አትገናኘው።

20 አባቱን ወይም እናቱን የሚሰድብ፥ በጽቅድቅ ጨለማ መብራቱ ይጠፋል።

21 በመጀመሪያ ፈጥኖ የተከማቸ ርስት ፍጻሜው አይባረክም።

22 ክፉ እመልሳለሁ አትበል፤ እግዚአብሔርን ተማመን፥ እርሱም ያድንሃል።

23 ሁለት ዓይነት ሚዛን በእግዚአብሔር ዘንድ አስጸያፊ ነው፥ ሐሰተኛ ሚዛንም መልካም አይደለም።

24 የሰው አካሄዱ ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው፤ እንግዲያስ ሰው መንገዱን እንዴት ያስተውላል?

25 ሰው በችኰላ። ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ነው ብሎ ቢሳል፥ ከተሳለም በኋላ ቢፀፀት ወጥመድ ነው።

26 ጠቢብ ንጉሥ ኀጥኣንን በመንሽ ይበትናቸዋል፥ መንኰራኵሩንም በእነርሱ ላይ ያንኰራኵርባቸዋል።

27 የሰው መንፈስ የእግዚአብሔር መብራት ነው የሆዱን ጕርጆች ሁሉ የሚመረምር።

28 ቸርነትና እውነት ንጉሥን ይጠብቁታል፤ ዙፋኑም በቸርነት ይበረታል።

29 የጎበዛዝት ክብር ጕልበታቸው ናት፥ የሽማግሌዎችም ጌጥ ሽበት ነው።

30 የሰንበር ቍስል ክፉዎችን ያነጻል፤ ግርፋትም ወደ ሆድ ጕርጆች ይገባል።