ምዕራፍ 29።

1፤ በሰባተኛውም ወር ከወሩ በመጀመሪያ ቀን የተቀደሰ ጉባኤ ይሁንላችሁ፤ የተግባርን ሥራ ሁሉ አትሥሩበት፤ መለከቶች የሚነፉበት ቀን ነው።

2፤ ለእግዚአብሔር ጣፋጭ ሽታ እንዲሆን የሚቃጠለውን መሥዋዕት፥ አንድ ወይፈን፥ አንድ አውራ በግ፥ ነውር የሌለባቸውን ሰባት የአንድ ዓመት ተባት የበግ ጠቦቶች፥

3፤ ለእህል ቍርባናቸው በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት፥ ለወይፈኑ ከመስፈሪያው ከአሥር እጅ ሦስት እጅ፥ ለአውራው በግ ከመስፈሪያው ከአሥር እጅ ሁለት እጅ፥

4፤ ለሰባቱ ጠቦቶች ለእያንዳንዱ ከመስፈሪያው አሥረኛ እጅ ታቀርባላችሁ።

5፤ ማስተስረያም የሚሆንላችሁን አንድ አውራ ፍየል ለኃጢአት መሥዋዕት ታቀርባላችሁ።

6፤ በወሩ መባቻ ከሚቃጠለው መሥዋዕትና ከእህሉ ቍርባን፥ በዘወትርም ከሚቃጠለው መሥዋዕትና ከእህሉ ቍርባን፥ ከመጠጡም ቍርባን ሌላ፥ እንደ ሕጋቸው ለእግዚአብሔር ጣፋጭ ሽታ እንዲሆን በእሳት የሚቀርቡ ናቸው።

7፤ ከዚህም ከሰባተኛው ወር በአሥረኛው ቀን የተቀደሰ ጉባኤ ይሁንላችሁ፤ ሰውነታችሁን አስጨንቁት፤ ከሥራ ሁሉ ምንም አታድርጉ።

8፤ ለእግዚአብሔርም ጣፋጭ ሽታ እንዲሆን የሚቃጠለውን መሥዋዕት፥ አንድ ወይፈን፥ አንድ አውራ በግ፥ ሰባት የአንድ ዓመት ተባት የበግ ጠቦቶች ታቀርባላችሁ፤ ነውር የሌለባቸው ይሁኑ።

9፤ ለእህል ቍርባናቸውም በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት፥ ለወይፈኑ ከመስፈሪያው ከአሥር እጅ ሦስት እጅ፥ ለአውራው በግ ከመስፈሪያው ከአሥር እጅ ሁለት እጅ፥

10፤ ለሰባቱ ጠቦቶች ለእያንዳንዱ ከመስፈሪያው አሥረኛ እጅ፥

11፤ ለኃጢአት መሥዋዕት አንድ አውራ ፍየል አቅርቡ። ከሚያስተሰርየው ከኃጢአት መሥዋዕት፥ በዘወትርም ከሚቃጠለው መሥዋዕትና ከእህሉ ቍርባን፥ ከመጠጥ ቍርባናቸውም ሌላ አቅርቡት።

12፤ ከሰባተኛውም ወር በአሥራ አምስተኛው ቀን የተቀደሰ ጉባኤ ይሁንላችሁ፤ የተግባርን ሥራ ሁሉ አትሥሩበት፥ ሰባት ቀንም ለእግዚአብሔር በዓል አድርጉ።

13፤ ለእግዚአብሔርም ጣፋጭ ሽታ እንዲሆን የሚቃጠለውን መሥዋዕት፥ አሥራ ሦስት ወይፈኖች፥ ሁለት አውራ በጎች፥ አሥራ አራት የአንድ ዓመት ተባት የበግ ጠቦቶች አቅርቡ፤ ነውር የሌለባቸውም ይሁኑ።

14፤ ለእህል ቍርባናቸውም በዘይት የተለወሰ መልካም ዱቄት፥ ለአሥራ ሦስት ወይፈኖች ለእያንዳንዱ ከመስፈሪያው ከአሥር እጅ ሦስት እጅ፥ ለሁለቱ አውራ በጎች ለእያንዳንዱ ከመስፈሪያው ከአሥር እጅ ሁለት እጅ፥

15፤ ለአሥራ አራቱ ጠቦቶች ለእያንዳንዱ ከመስፈሪያው አሥረኛ እጅ፥

16፤ ለኃጢአትም መሥዋዕት አንድ አውራ ፍየል ታቀርባላችሁ፤ በዘወትር ከሚቃጠለው መሥዋዕትና ከእህሉ ቍርባን ከመጠጡም ቍርባን ሌላ የሚቀርቡ ናቸው።

17፤ በሁለተኛውም ቀን አሥራ ሁለት ወይፈኖችን፥ ሁለት አውራ በጎችን፥ ነውር የሌለባቸው አሥራ አራት የአንድ ዓመት ተባት የበግ ጠቦቶችን፥

18፤ ለወይፈኖቹና ለአውራ በጎቹ ለጠቦቶቹም የእህል ቍርባናቸውንና የመጠጥ ቍርባናቸውን እንደ ቍጥራቸው መጠን እንደ ሕጉ፥

19፤ ለኃጢአትም መሥዋዕት አንድ አውራ ፍየልን ታቀርባላችሁ፤ በዘወትር ከሚቃጠለው መሥዋዕትና ከእህሉ ቍርባን ከመጠጡም ቍርባናቸው ሌላ የሚቀርቡ ናቸው።

20፤ በሦስተኛውም ቀን አሥራ አንድ ወይፈኖች፥ ሁለት አውራ በጎች፥ ነውር የሌለባቸውን አሥራ አራት የአንድ ዓመት ተባት የበግ ጠቦቶች፥

21፤ ለወይፈኖቹና ለአውራ በጎቹ ለጠቦቶቹም የእህል ቍርባናቸውንና የመጠጥ ቍርባናቸውን እንደ ቍጥራቸው መጠን እንደ ሕጉ፥

22፤ ለኃጢአትም መሥዋዕት አንድ አውራ ፍየል፥ በዘወትር ከሚቃጠለው መሥዋዕትና ከእህሉ ቍርባን ከመጠጡም ቍርባን ሌላ ታቀርባላችሁ።

23፤ በአራተኛውም ቀን አሥር ወይፈኖች፥ ሁለት አውራ በጎች፥ ነውር የሌለባቸውን አሥራ አራት የአንድ ዓመት ተባት የበግ ጠቦቶች፥

24፤ ለወይፈኖቹና ለአውራ በጎቹ ለጠቦቶቹም የእህል ቍርባናቸውንና የመጠጥ ቍርባናቸውን እንደ ቍጥራቸውም መጠን እንደ ሕጉ፥

25፤ ለኃጢአትም መሥዋዕት አንድ አውራ ፍየል፥ በዘወትር ከሚቃጠለው መሥዋዕትና ከእህሉ ቍርባን ከመጠጡም ቍርባን ሌላ ታቀርባላችሁ።

26፤ በአምስተኛውም ቀን ዘጠኝ ወይፈኖች፥ ሁለት አውራ በጎች፥ ነውር የሌለባቸውን አሥራ አራት የአንድ ዓመት ተባት የበግ ጠቦቶች፥

27፤ ለወይፈኖቹና ለአውራ በጎቹ ለጠቦቶቹም የእህል ቍርባናቸውንና የመጠጥ ቍርባናቸውን እንደ ቍጥራቸው መጠን እንደ ሕጉ፥

28፤ ለኃጢአትም መሥዋዕት አንድ አውራ ፍየል፥ በዘወትር ከሚቃጠለው መሥዋዕትና ከእህሉ ቍርባን ከመጠጡም ቍርባን ሌላ ታቀርባላችሁ።

29፤ በስድስተኛውም ቀን ስምንት ወይፈኖች፥ ሁለት አውራ በጎች፥ ነውር የሌለባቸውን አሥራ አራት የአንድ ዓመት ተባት የበግ ጠቦቶች፥

30፤ ለወይፈኖቹና ለአውራ በጎቹ ለጠቦቶቹም የእህል ቍርባናቸውንና የመጠጥ ቍርባናቸውን እንደ ቍጥራቸው መጠን እንደ ሕጉ፥

31፤ ለኃጢአትም መሥዋዕት አንድ አውራ ፍየል፥ በዘወትር ከሚቃጠለው መሥዋዕትና ከእህሉ ቍርባን ከመጠጡም ቍርባን ሌላ ታቀርባላችሁ።

32፤ በሰባተኛውም ቀን ሰባት ወይፈኖች፥ ሁለት አውራ በጎች፥ ነውር የሌለባቸውን አሥራ አራት የአንድ ዓመት ተባት የበግ ጠቦቶች፥

33፤ ለወይፈኖቹና ለአውራ በጎቹ ለጠቦቶቹም የእህል ቍርባናቸውንና የመጠጥ ቍርባናቸውን እንደ ቍጥራቸው መጠን እንደ ሕጉ፥

34፤ ለኃጢአትም መሥዋዕት አንድ አውራ ፍየል፥ በዘወትር ከሚቃጠለው መሥዋዕትና ከእህሉ ቍርባን ከመጠጡም ቍርባን ሌላ ታቀርባላችሁ።

35፤ በስምንተኛውም ቀን የተቀደሰ ጉባኤ ይሁንላችሁ፤ የተግባርን ሥራ ሁሉ አትሥሩበት።

36፤ ለእግዚአብሔርም ጣፋጭ ሽታ እንዲሆን በእሳት የሚቃጠለውን መሥዋዕት፥ አንድ ወይፈን፥ አንድ አውራ በግ፥ ነውር የሌለባቸውን ሰባት የአንድ ዓመት ተባት የበግ ጠቦቶች ታቀርባላችሁ።

37፤ የእህል ቍርባናቸውና የመጠጥ ቍርባናቸው ለወይፈኑ ለአውራውም በግ ለጠቦቶቹም እንደ ቍጥራቸው መጠን እንደ ሕጉ ይሆናሉ።

38፤ ለኃጢአትም መሥዋዕት አንድ አውራ ፍየል ታቀርባላችሁ፤ በዘወትር ከሚቃጠለው መሥዋዕትና ከእህሉ ቍርባን ከመጠጡም ቍርባን ሌላ የሚቀርቡ ናቸው።

39፤ እነዚህንም፥ ከስእለታችሁና በፈቃዳችሁ ከምታመጡት ሌላ፥ ለሚቃጠል መሥዋዕት፥ ለእህልም ለመጠጥም ቍርባን፥ ለደኅንነትም መሥዋዕታችሁ በበዓላችሁ ጊዜ ለእግዚአብሔር አቅርቡ።

40፤ ሙሴም ለእስራኤል ልጆች እግዚአብሔር ሙሴን ያዘዘውን ሁሉ ነገራቸው።