ምዕራፍ 24።

1፤ በለዓምም እግዚአብሔር እስራኤልን ይባርክ ዘንድ እንዲወድድ ባየ ጊዜ፥ አስቀድሞ ያደርግ የነበረውን አስማት ይሻ ዘንድ አልሄደም፤ ነገር ግን ወደ ምድረ በዳ ፊቱን አቀና።

2፤ በለዓምም ዓይኑን አንሥቶ እስራኤል በየነገዱ ተቀምጦ አየ፤ የእግዚአብሔርም መንፈስ በላዩ መጣ።

3፤ ምሳሌውን ይመስል ጀመር፥ እንዲህም አለ።

የቢዖር ልጅ በለዓም እንዲህ ይላል፥

ዓይኖቹ የተከፈቱለት ሰው እንዲህ ይላል፤

4፤ የእግዚአብሔርን ቃል የሚሰማ፥

ሁሉን የሚችል የአምላክን ራእይ የሚያይ፥

የወደቀው፥ ዓይኖቹም የተከፈቱለት እንዲህ ይላል።

5፤ ያዕቆብ ሆይ፥ ድንኳኖችህ፥

እስራኤል ሆይ ማደሪያዎችህ ምንኛ ያምራሉ!

6፤ እንደ ሸለቆች፥

በወንዝ ዳር እንዳሉ አትክልቶች፥

እግዚአብሔር እንደ ተከለው እሬት

በውኃም ዳር እንዳሉ ዝግባዎች ተዘርግተዋል።

7፤ ከማድጋዎቹ ውኃ ይፈስሳል፥

ዘሩም በብዙ ውኆች ይሆናል፥

ንጉሡም ከአጋግ ይልቅ ከፍ ከፍ ይላል፥ መንግሥቱም ይከበራል።

8፤ እግዚአብሔርም ከግብፅ አውጥቶታል፤

ጕልበቱ አንድ ቀንድ እንዳለው ነው፤

ጠላቶቹን አሕዛብን ይበላል፥

አጥንቶቻቸውንም ይሰባብራል፥

በፍላጾቹም ይወጋቸዋል።

9፤ እንደ አንበሳ ዐርፎ ተኝቶአል፥

እንደ እንስቲቱም አንበሳ ተጋድሞአል፤

ማን ያስነሣዋል?

የሚመርቅህ ሁሉ የተመረቀ ይሁን፥

የሚረግምህም ሁሉ የተገመ ይሁን።

10፤ የባላቅም ቍጣ በበለዓም ላይ ነደደ፤ እጆቹንም አጨበጨበ፤ ባላቅም በለዓምን። ጠላቶቼን ትረግም ዘንድ ጠራሁህ፥ እነሆም፥ ሦስት ጊዜ ፈጽመህ መረቅሃቸው፤ አሁንም እንግዲህ ወደ ስፍራህ ሽሽ፤

11፤ እኔ አከብርህ ዘንድ ወድጄ ነበር፤ እግዚአብሔር ግን፥ እነሆ፥ ክብርህን ከለከለ አለው።

12፤13፤ በለዓምም ባላቅን አለው። ባላቅ በቤቱ የሞላውን ብርና ወርቅ ቢሰጠኝ፥ መልካሙን ወይም ክፉውን ከልቤ ለማድረግ የእግዚአብሔርን ቃል እተላለፍ ዘንድ አይቻለኝም፤ እግዚአብሔር የተናገረውን እርሱን እናገራለሁ ብዬ ወደ እኔ ለላክሃቸው መልእክተኞች አልተናገርኋቸውምን?

14፤ አሁንም፥ እነሆ፥ ወደ ሕዝቤ እሄዳለሁ፤ ና፥ ይህ ሕዝብ በኋለኛው ዘመን በሕዝብህ ላይ የሚያደርገውን እነግርሃለሁ።

15፤ ምሳሌውንም ይመስል ጀመር፥ እንዲህም አለ።

የቢዖር ልጅ በለዓም እንዲህ ይላል፥

ዓይኖቹም የተከፈቱለት ሰው እንዲህ ይላል፤

16፤ የእግዚአብሔርን ቃል የሚሰማ፥

የልዑልንም እውቀት የሚያውቅ፥

ሁሉን የሚችል የአምላክን ራእይ የሚያይ፥

የወደቀው፥ ዓይኖቹም የተከፈቱለት እንዲህ ይላል።

17፤ አየዋለሁ፥ አሁን ግን አይደለም፤

እመለከተዋለሁ፥ በቅርብ ግን አይደለም፤

ከያዕቆብ ኮከብ ይወጣል፥

ከእስራኤል በትር ይነሣል፥

የሞዓብንም ማዕዘኖች ይመታል፥

የሤትንም ልጆች ያጠፋል።

18፤ ኤዶምያስም ርስቱ ይሆናል፥

ጠላቱ ሴይር ደግሞ ርስቱ ይሆናል፤

እስራኤልም በኃይል ያደርጋል።

19፤ ከያዕቆብም የሚወጣ ገዥ ይሆናል፥

ከከተማውም የቀሩትን ያጠፋል።

20፤ አማሌቅንም አይቶ ምሳሌውን ይመስል ጀመር፥ እንዲህም አለ።

አማሌቅ የአሕዛብ አለቃ ነበረ፤

ፍጻሜው ግን ወደ ጥፋት ይመጣል።

21፤ ቄናውያንንም አይቶ ምሳሌውን ይምስል ጀመር፥ እንዲህም አለ።

ማደሪያህ የጸና ነው፥

ጎጆህም በአምባ ላይ ተሠርቶአል፤

22፤ ነገር ግን አሦር እስኪማርክህ ድረስ ቄናዊው ለጥፋት ይሆናል።

23፤ ምሳሌውንም ይመስል ጀመር፥ እንዲህም አለ።

እግዚአብሔር ይህን ሲያደርግ

አወይ! ማን በሕይወት ይኖራል?

24፤ ከኪቲም ዳርቻ መርከቦች ይመጣሉ፥

አሦርንም ያስጨንቃሉ፥

ዔቦርንም ያስጨንቃሉ፤

እርሱም ደግሞ ወደ ጥፋት ይመጣል።

25፤ በለዓምም ተነሣ፥ ተመልሶም ወደ ስፍራው ሄደ፤ ባላቅም ደግሞ መንገዱን ሄደ።