ምዕራፍ 34።

1፤ ኤሊሁም ደግሞ መለሰ፥ እንዲህም አለ።

2፤ እናንተ ጥበበኞች፥ ቃሌን ስሙ፤

እናንተም አዋቂዎች፥ ወደ እኔ አድምጡ።

3፤ ትናጋ መብልን እንደሚቀምስ፥

ጆሮ ቃልን ትለያለችና።

4፤ ቅን የሆነውን ነገር እንምረጥ፤

መልካሙንም ነገር በመካከላችን እንወቅ።

5፤ ኢዮብ። እኔ ጻድቅ ነኝ፥

እግዚአብሔር ግን ፍርዴን አስወገደ፤

6፤ ምንም እውነተኛ ብሆን እንደ ውሸተኛ ተቈጠርሁ፤

ምንም ባልበድል ቍስሌ የማይፈወስ ነው ብሎአል።

7፤8፤9፤ ኢዮብም። በእግዚአብሔር መደሰት

ለሰው ምንም አይጠቅምም ብሎአልና

ከበደለኞች ጋር የሚተባበር፥

ክፉ ከሚያደርጉስ ጋር የሚሄድ፥

መሳለቅን እንደ ውኃ የሚጠጣት

እንደ ኢዮብ ያለ ሰው ማን ነው?

10፤ ስለዚህ እናንተ አእምሮ ያላችሁ ሰዎች፥ ስሙኝ፤

ክፋትን ያደርግ ዘንድ ከእግዚአብሔር፥

በደልንም ይሠራ ዘንድ ሁሉን ከሚችል አምላክ ይራቅ።

11፤ ለሰው ሥራውን ይመልስለታል፥

ሰውም እንደ መንገዱ ያገኝ ዘንድ ያደርጋል።

12፤ በእውነት እግዚአብሔር ክፉ አይሠራም፥

ሁሉንም የሚችል አምላክ ፍርድን ጠማማ አያደርግም።

13፤ ምድርን አደራ የሰጠው ማን ነው?

ዓለምንስ ሁሉ በእርሱ ላይ ያኖረ ማን ነው?

14፤ እርሱ ልቡን ወደ ራሱ ቢመልስ፥

መንፈሱንና እስትንፋሱን ወደ ራሱ ቢሰበስብ፥

15፤ ሥጋ ለባሽ ሁሉ በአንድነት ይጠፋል፥

ሰውም ወደ አፈር ይመለሳል።

16፤ አስተዋይ ብትሆን ይህን ስማ፤

የንግግሬንም ቃል አድመጥ።

17፤ በውኑ ጽድቅን የሚጠላ ይሠለጥናልን?

ጻድቅና ኃያል የሆነውስ በደለኛ ታደርገዋለህን?

18፤ ማንም ሰው ንጉሡን። በደለኛ ነህ፥

መኳንንቱንም። ክፉዎች ናችሁ ይላልን?

19፤ እነርሱ ሁሉ የእጁ ሥራ ናቸውና

በአለቆች ፊት አያደላም፥

ባለጠጋውንም ሰው ከድሀው ይበልጥ አይመለከትም።

20፤ እነርሱ በመንፈቀ ሌሊት በድንገት ይሞታሉ፤

ሕዝቡ ተንቀጥቅጦ ያልፋል፥

ኃያላንም ያለ እጅ ይነጠቃሉ።

21፤ ዓይኖቹ በሰው መንገድ ላይ ናቸው፥

እርምጃውንም ሁሉ ያያል።

22፤ ኃጢአትን የሚሠሩ ይሰወሩበት ዘንድ

ጨለማ ወይም የሞት ጥላ የለም።

23፤ ሰው በእግዚአብሔር ፊት ለመፈራረድ እንዲመጣ

ጊዜ አይወሰንለትም።

24፤ ታላላቆችን ያለ ምርመራ ይሰባብራል፥

በእነርሱም ፋንታ ሌሎችን ያቆማል።

25፤ ሥራቸውን ያውቃል፤

እንዲደቅቁም በሌሊት ይገለባብጣቸዋል።

26፤ ሰዎች እያዩ እንደ ክፉዎች ይመታቸዋል፤

27፤28፤ የድሀውን ልቅሶ ወደ እርሱ ያደርሱ ዘንድ፥

እርሱም የችግረኛውን ድምፅ ይሰማ ዘንድ፥

እርሱን ከመከተል ፈቀቅ ብለዋልና፥

ከመንገዱም ሁሉ አንዱን አልተመለከቱምና።

29፤ በሕዝብ ወይም በሰው ዘንድ ቢሆን፥

እርሱ ቢያሳርፍ የሚፈርድ ማን ነው?

ፊቱንስ ቢሰውር የሚያየው ማን ነው?

30፤ ይህም ዝንጉ ሰው እንዳይነግሥ፥

ሕዝቡም የሚያጠምድ እንዳይኖር ነው።

31፤ እግዚአብሔርን። እኔ ሳልበድል ቅጣት ተቀበልሁ፤

32፤ የማላየውን ነገር አንተ አስተምረኝ፤

ኃጢአትንም ሠርቼ እንደ ሆነ፥

ደግሜ አልሠራም የሚለው ማን ነው?

33፤ በውኑ አንተ ጥለኸዋልና

ፍዳው አንተ እንደምትወድደው ይሆናልን?

አንተ ትመርጣለህ እንጂ እኔ አይደለሁም፤

ስለዚህ የምታውቀውን ተናገር።

34፤ የሚሰሙኝ ጥበበኞች ሁሉ፥

አስተዋዮችም እንዲህ ይሉኛል።

35፤ ኢዮብ ያለ እውቀት ተናግሮአል፥

ቃሉም በአእምሮ አይደለችም።

36፤ ኢዮብ እስከ ፍጻሜ ድረስ ምነው በተፈተነ ኖሮ!

እርሱ እንደ ክፉዎች መልሶአልና፤

37፤ በኃጢአቱም ላይ ዓመፅን ጨምሮአልና፥

በእኛም መካከል በእጁ ያጨበጭባልና፥

ቃልንም በእግዚአብሔር ላይ ያበዛልና።