ምዕራፍ 33።

1፤ ነገር ግን፥ ኢዮብ ሆይ፥ ንግግሬን እንድትሰማ፥

ቃሌንም ሁሉ እንድታደምጥ እለምንሃለሁ።

2፤ እነሆ፥ አፌን ከፍቻለሁ፥

አንደበቴም በትናጋዬ ተናግሮአል።

3፤ ቃሌ የልቤን ቅንነት ያወጣል፤

ከንፈሮቼም የሚያውቁትን በቅንነት ይናገራሉ።

4፤ የእግዚአብሔር መንፈስ ፈጠረኝ፥

ሁሉንም የሚችል የአምላክ እስትንፋስ ሕይወት ሰጠኝ።

5፤ ይቻልህ እንደ ሆነ መልስልኝ፤

ቃልህንም አዘጋጅተህ በፊቴ ቁም።

6፤ እነሆ፥ በእግዚአብሔር ፊት እኔ እንደ አንተ ነኝ፤

እኔ ደግሞ ከጭቃ የተፈጠርሁ ነኝ።

7፤ እነሆ፥ ግርማዬ አታስፈራህም

እጄም አትከብድብህም።

8፤ በጆሮዬ ተናግረሃል፥

የቃልህንም ድምፅ ሰምቻለሁ፥ እንዲህም ብለሃል።

9፤ እኔ ያለ መተላለፍ ንጹሕ ነኝ፤

ያለ ነውር ነኝ፥ ኃጢአትም የለብኝም፤

10፤ እነሆ፥ ምክንያት አግኝቶብኛል፥

እንደ ጠላቱም ቈጥሮኛል፤

11፤ እግሬን በግንድ አጣበቀ፥

መንገዴንም ሁሉ ተመለከተ።

12፤ እነሆ፥ አንተ በዚህ ጻድቅ አይደለህም፤

እግዚአብሔር ከሰው ይበልጣል ብዬ እመልስልሃለሁ።

13፤ አንተ። ለቃሌ ሁሉ አይመልስልኝም ብለህ፥

ስለ ምን ከእርሱ ጋር ትከራከራለህ?

14፤ እግዚአብሔር በአንድ መንገድ በሌላም ይናገራል፤

ሰው ግን አያስተውለውም።

15፤ በሕልም፥ በሌሊት ራእይ፥

አፍላ እንቅልፍ በሰዎች ላይ ሲወድቅ፥

በአልጋ ላይ ተኝተው ሳሉ፥

16፤ በዚያን ጊዜ የሰዎችን ጆሮ ይከፍታል፥

በተግሣጹም ያስደነግጣቸዋል፥

17፤ ሰውን ከክፉ ሥራው ይመልሰው ዘንድ

ከሰውም ትዕቢትን ይሰውር ዘንድ፤

18፤ ነፍሱን ከጕድጓድ፥

በሰይፍም እንዳይጠፋ ሕይወቱን ይጠብቃል።

19፤ ደግሞ በአልጋ ላይ በደዌ ይገሥጸዋል፥

አጥንቱንም ሁሉ ያደነዝዛል።

20፤ ሕይወቱም እንጀራን፥

ነፍሱም ጣፋጭ መብልን ትጠላለች።

21፤ ሥጋው እስከማይታይ ድረስ ይሰለስላል፤

ተሸፍኖ የነበረውም አጥንት ይገለጣል።

22፤ ነፍሱ ወደ ጕድጓዱ፥

ሕይወቱም ወደሚገድሉአት ቀርባለች።

23፤ የቀናውን መንገድ ለሰው ያስታውቀው ዘንድ፥

ከሺህ አንድ ሆኖ የሚተረጕም መልአክ ቢገኝለት፥

24፤ እየራራለት።

ቤዛ አግኝቻለሁና

ወደ ጕድጓድ እንዳይወርድ አድነው ቢለው፥

25፤ ሥጋው እንደ ሕፃን ሥጋ ይለመልማል፤

ወደ ጕብዝናውም ዘመን ይመለሳል።

26፤ ወደ እግዚአብሔር ይጸልያል፥

እርሱም ሞገስን ይሰጠዋል

ፊቱንም በደስታ ያሳየዋል፤

ለሰውም ጽድቁን ይመልስለታል።

27፤ እርሱም በሰው ፊት እየዘመረ።

እኔ በድያለሁ፥ ቅኑንም አጣምሜአለሁ፤

የሚገባኝንም ብድራት አልተቀበልሁም፤

28፤ ነፍሴ ወደ ጕድጓድ እንዳትወርድ አድኖአታል፥

ሕይወቴም ብርሃንን ታያለች ይላል።

29፤ እግዚአብሔር ይህን ሁሉ

ሁለት ጊዜና ሦስት ጊዜ ከሰው ጋር ያደርጋል፤

30፤ ይህም ነፍሱን ከጕድጓድ ይመልስ ዘንድ፥

በሕያዋንም ብርሃን ያበራ ዘንድ ነው።

31፤ ኢዮብ ሆይ፥ አድምጥ፥ እኔንም ስማ፤

ዝም በል፥ እኔም እናገራለሁ።

32፤ ነገር ቢኖርህ መልስልኝ፤

ትጸድቅ ዘንድ እወድዳለሁና ተናገር።

33፤ ያለዚያም እኔን ስማ፤

ዝም በል፥ እኔም ጥበብን አስተምርሃለሁ።