ምዕራፍ 18።

1፤ ሹሐዊውም በልዳዶስ መለሰ እንዲህም አለ።

2፤ እስከ መቼ ቃልን ታጠምዳለህ?

አስተውል፥ ከዚያም በኋላ እንናገራለን።

3፤ ስለ ምንስ እንደ እንስሶች ተቈጠርን?

ስለ ምንስ በዓይንህ ፊት ረከስን?

4፤ ቍጣ ወርሶሃል፤ አንተስ የሞትህ እንደ ሆነ፥

ምድር ስለ አንተ ባድማ ትሆናለችን?

ወይስ ዓለት ከስፍራው ይነቀላልን?

5፤ የኃጢአተኛ መብራት ይጠፋል፥

የእሳቱም ነበልባል ብልጭ አይልም።

6፤ ብርሃን በድንኳኑ ውስጥ ይጨልማል፥

መብራቱም በላዩ ይጠፋል።

7፤ የኃይሉም እርምጃ ትጠብባለች፥

ምክሩም ትጥለዋለች።

8፤ እግሩ በወጥመድ ትያዛለች፥

በመረብም ላይ ይሄዳል።

9፤ አሽክላ ሰኰናውን ይይዛል፥

ወስፈንጠርም ይበረታበታል።

10፤ በምድር ላይ የሸምቀቆ ገመድ፥

በመንገዱም ላይ ወጥመድ ለእርሱ ተሰውራለች።

11፤ ድንጋጤ በዙሪያው ታስፈራዋለች፥

በስተ ኋላውም ሆና ታባርራቸዋለች።

12፤ ኃይሉ በራብ ትደክማለች፥

መቅሠፍትም እስኪሰናከል ተዘጋጅቶለታል።

13፤ የሰውነቱ ብልቶች ይጠፋሉ፤

የሞትም በኵር ልጅ ብልቶቹን ይበላል።

14፤ ከሚታመንበት ድንኳን ይነቀላል፤

ወደ ድንጋጤም ንጉሥ ያስቸኵሉታል።

15፤ በድንኳኑ ውስጥ ለእርሱ የማይሆነው ይኖራል፤

በመኖሪያውም ላይ ዲን ይበተናል።

16፤ ሥሩ ከበታቹ ይደርቃል፥

ጫፉም ከበላይ ይረግፋል።

17፤ መታሰቢያው ከምድር ላይ ይጠፋል፥

በሜዳም ስም አይቀርለትም።

18፤ ከብርሃን ወደ ጨለማ ያፈልሱታል፥

ከዓለምም ያሳድዱታል።

19፤ ዘርም ትውልድም በሕዝቡ መካከል አይሆንለትም፤

በመኖሪያውም ውስጥ የሚቀመጥ ሰው አይቀርለትም።

20፤ የፊተኞች ሰዎች እንደ ደነገጡ፥

እንዲሁ የኋለኞች ሰዎች ስለ ዘመኑ ይደነቃሉ።

21፤ በእውነት የኃጢአተኞች ቤት እንዲሁ ናት፥

እግዚአብሔርንም የማያውቅ ሰው ስፍራ ይህ ነው።