ምዕራፍ 9።

1፤ ኢዮብም መለሰ እንዲህም አለ።

2፤ በእውነት እንዲህ እንደ ሆነ አወቅሁ፤

ሰውስ በእግዚአብሔር ፊት ጻድቅ መሆን እንዴት ይችላል?

3፤ ከእርሱ ጋር ይከራከር ዘንድ ቢወድድ፥

ከሺህ ነገር አንዱን መመለስ አይችልም።

4፤ ልቡ ጠቢብ፥ ኃይሉም ታላቅ ነው፤

ደፍሮትስ በደኅና የሄደ ማን ነው?

5፤ ተራሮችን ይነቅላል፤ አያውቁትም፤

በቍጣውም ይገለብጣቸዋል።

6፤ ምድርን ከስፍራው ያናውጣታል፥

ምሰሶችዋም ይንቀጠቀጣሉ።

7፤ ፀሐይን ያዝዛታል፥ አትወጣምም፤

ከዋክብትንም ያትማል።

8፤ ሰማያትን ብቻውን ይዘረጋል፥

በባሕሩም ማዕበል ላይ ይረግጣል።

9፤ ድብ የሚባለውን ኮከብና ኦሪዮን የሚባለውን ኮከብ፥ ሰባቱንም ከዋክብት፥

በደቡብም በኩል ያሉትን የከዋክብት ማደርያዎች ሠርቶአል።

10፤ የማይመረመረውን ታላላቅ ነገር፥

የማይቈጠረውንም ተአምራት ያደርጋል።

11፤ እነሆ፥ ቢመጣብኝ አላየውም፤

ቢያልፍብኝም አላውቀውም።

12፤ እነሆ፥ ፈጥኖ ቢነጥቅ የሚከለክለው ማን ነው?

እርሱንስ። ምን ታደርጋለህ? የሚለው ማን ነው?

13፤ እግዚአብሔር ቍጣውን አይመልስም፤

ከእርሱ በታች ረዓብን የሚረዱ ይዋረዳሉ።

14፤ ይልቁንስ እመልስለት ዘንድ፥

ቃሌንስ በፊቱ እመርጥ ዘንድ እኔ ማን ነኝ?

15፤ ጻድቅ ብሆን ኖሮ አልመልስለትም ነበር፤

ወደ ፈራጄም እለምን ነበር።

16፤ ብጠራው እርሱም ቢመልስልኝ ኖሮ፥

ቃሌን እንደ ሰማ አላምንም ነበር።

17፤ በዐውሎ ነፋስ ይሰብረኛል፥

ቍስሌንም ያለ ምክንያት ያበዛል።

18፤ እተነፍስ ዘንድ አይተወኝም፥

ነገር ግን መራራን ነገር አጥግቦኛል።

19፤ የኃይል ነገር ቢሆን እርሱ ኃያል ነው፤

የፍርድ ነገር ቢሆን። ጊዜን ወሳኙ ማን ነው? ይላል።

20፤ ጻድቅ ብሆን አፌ ይወቅሰኛል፤

ፍጹምም ብሆን ጠማማ ያደርገኛል።

21፤ ፍጹም ነኝ ራሴንም አልመለከትም፤

ሕይወቴንም እንቃታለሁ።

22፤ ይህ ሁሉ አንድ ነው፤ ስለዚህ።

ፍጹማንንና ክፉዎችን ያጠፋል እላለሁ።

23፤ መቅሠፍቱ ፈጥኖ ቢገድል፥

በንጹሐን ፈተና ይሳለቃል።

24፤ ምድር በኃጥአን እጅ ተሰጥታለች፤

የፈራጆችዋን ፊት ሸፍኖአል፤

እርሱ ካልሆነ ማን ነው?

25፤ ዘመኔ ከሚሮጥ ሰው ይልቅ ይፈጥናል፤

ይሸሻል፥ መልካምንም አያይም።

26፤ የደንገል ታንኳ እንደሚፈጥን፥

ንስርም ወደ ንጥቂያው እንደሚበርር ያልፋል።

27፤ እኔ። የኀዘን እንጕርጕሮዬን እረሳለሁ፤

ፊቴን መልሼ እጽናናለሁ ብል፥

28፤ ንጹሕ እንደማታደርገኝ እኔ አውቃለሁና

ከመከራዬ ሁሉ እፈራለሁ።

29፤ በደለኛ እንደሚሆን ሰው እሆናለሁ፤

ስለ ምንስ በከንቱ እደክማለሁ?

30፤ በአመዳይ ውስጥ ብታጠብ፥

እጆቼንም እጅግ ባነጻ፥

31፤ በአዘቅት ውስጥ ታሰጥመኛለህ፥

ልብሴም ይጸየፈኛል።

32፤ እንድመልስለት አብረን ወደ ፍርድ እንገባ ዘንድ፥

እርሱ እንደ እኔ ሰው አይደለም።

33፤ እጁን በሁለታችን ላይ የሚያኖር ዳኛ

በመካከላችን ምነው በተገኘ!

34፤ በትሩን ከእኔ ላይ ያርቅ፥

ግርማውም አያስፈራኝ፤

35፤ እናገርም ነበር፥ አልፈራውምም ነበር፤

በራሴ እንዲህ አይደለሁምና።