ምዕራፍ 17።

1፤ በተራራማውም በኤፍሬም አገር ሚካ የተባለ አንድ ሰው ነበረ።

2፤ እናቱንም። ከአንቺ ዘንድ የተወሰደው፥ የረገምሽበትም፥ በጆሮዬም የተናገርሽበት አንድ ሺህ አንድ መቶ ብር፥ እነሆ፥ በእኔ ዘንድ አለ፤ እኔም ወስጄዋለሁ አላት። እናቱም። ልጄ ሆይ፥ እግዚአብሔር ይባርክህ አለችው።

3፤ አንዱን ሺህ አንዱን መቶ ብርም መለሰላት፤ እናቱም። ይህን ብር የተቀረጸ ምስልና ቀልጦ የተሠራ ምስል አድርጌ ከእጄ ስለ ልጄ ለእግዚአብሔር እቀድሰዋለሁ፤ አሁንም ለአንተ እመልሰዋለሁ አለች።

4፤ ለእናቱም ገንዘቡን በመለሰላት ጊዜ እናቱ ሁለቱን መቶ ብር ወስዳ ለአንጥረኛ ሰጠችው፥ እርሱም የተቀረጸ ምስልና ቀልጦ የተሠራ ምስል አደረገው። ያም በሚካ ቤት ነበረ።

5፤ ሰውዮውም ሚካ የአምላክ ቤት ነበረው፤ ኤፉድና ተራፊም አደረገ፥ ከልጆቹም አንዱን ቀደሰው፥ ካህንም ሆነለት።

6፤ በዚያም ዘመን በእስራኤል ዘንድ ንጉሥ አልነበረም፤ ሰውም ሁሉ በፊቱ መልካም መስሎ የታየውን ያደርግ ነበር።

7፤ በቤተ ልሔም ይሁዳም ከይሁዳ ወገን የሆነ አንድ ጕልማሳ ነበረ፥ እርሱም ሌዋዊ ነበረ፥ በዚያም ይቀመጥ ነበር።

8፤ ይህም ሰው የሚቀመጥበትን ስፍራ ለመሻት ከከተማው ከቤተ ልሔም ይሁዳ ወጣ፤ ሲሔድም ወደ ተራራማው ወደ ኤፍሬም አገር ወደ ሚካ ቤት መጣ።

9፤ ሚካም። ከወዴት መጣህ? አለው። እርሱም። ከቤተ ልሔም ይሁዳ የሆንሁ ሌዋዊ ነኝ፤ የምቀመጥበትንም ስፍራ ለመሻት እሄዳለሁ አለው።

10፤ ሚካም። ከእኔ ዘንድ ተቀመጥ፥ አባትና ካህንም ሁነኝ፤ እኔም ልብሶችንና ምግብህን፥ በእየዓመቱም አሥር ብር እሰጥሃለሁ አለው። ሌዋዊውም ገባ።

11፤ ሌዋዊውም ከሰውዮው ጋር መቀመጥን ፈቀደ፤ ጕልማሳውም ከልጆቹ እንደ አንዱ ሆነለት።

12፤ ሚካም ሌዋዊውን ቀደሰ፥ ጕልማሳውም ካህኑ ሆነለት፥ በሚካም ቤት ነበረ።

13፤ ሚካም። ሌዋዊ ካህን ስለ ሆነልኝ እግዚአብሔር መልካም እንዲሠራልኝ አሁን አውቃለሁ አለ።