ምዕራፍ 14።

1፤ ሶምሶንም ወደ ተምና ወረደ፥ በተምናም ከፍልስጥኤማውያን ልጆች አንዲት ሴት አየ።

2፤ ወጥቶም ለአባቱና ለእናቱ። በተምና ከፍልስጥኤማውያን ልጆች አንዲት ሴት አይቻለሁ፤ አሁንም እርስዋን አጋቡኝ አላቸው።

3፤ አባቱና እናቱም። ካልተገረዙት ከፍልስጥኤማውያን ሚስት ለማግባት ትሄድ ዘንድ ከወንድሞችህ ሴቶች ልጆች ከሕዝቤም ሁሉ መካከል ሴት የለምን? አሉት። ሶምሶንም አባቱን። ለዓይኔ እጅግ ደስ አሰኝታኛለችና እርስዋን አጋባኝ አለው።

4፤ እግዚአብሔርም በፍልስጥኤማውያን ላይ ምክንያት ይፈልግ ነበርና ነገሩ ከእርሱ ሆነ፤ አባቱና እናቱ ግን አላወቁም። በዚያን ጊዜም ፍልስጥኤማውያን በእስራኤል ላይ ገዦች ነበሩ።

5፤ ሶምሶንም አባቱና እናቱም ወደ ተምና ወረዱ፥ በተምናም ወዳለው ወደ ወይኑ ስፍራ መጡ፤ እነሆም፥ የአንበሳ ደቦል እያገሣ ወደ እርሱ ደረሰ።

6፤ የእግዚአብሔርም መንፈስ በእርሱ ላይ በኃይል ወረደ፤ ጠቦትን እንደሚቆራርጥ በእጁ ምንም ሳይኖር ቈራረጠው፤ ያደረገውንም ለአባቱና ለእናቱ አልነገረም።

7፤ ወርዶም ከሴቲቱ ጋር ተነጋገረ፤ እጅግም ደስ አሰኘችው።

8፤ ከጥቂትም ቀን በኋላ ሊያገባት ተመለሰ፥ የአንበሳውንም ሬሳ ያይ ዘንድ ከመንገድ ፈቀቅ አለ፤ እነሆም፥ በአንበሳው ሬሳ ውስጥ ንብ ሰፍሮበት ነበር፥ ማርም ነበረበት።

9፤ በእጁም ወስዶ መንገድ ለመንገድ እየበላ ሄደ፤ ወደ አባቱና ወደ እናቱ መጣ፥ ማሩንም ሰጣቸው፥ እነርሱም በሉ፤ ማሩንም ከአንበሳው ሬሳ ውስጥ እንደ ወሰደ አልነገራቸውም።

10፤ አባቱም ወደ ሴቲቱ ወረደ፤ ጎበዞችም እንዲህ ያደርጉ ነበርና ሶምሶን በዚያ በዓል አደረገ።

11፤ ባዩትም ጊዜ ከእርሱ ጋር ይሆኑ ዘንድ ሌሎች ሠላሳ ሰዎች ሰጡት።

12፤ ሶምሶንም። እንቆቅልሽ ልስጣችሁ፤ በሰባቱም በበዓሉ ቀኖች ውስጥ ፈትታችሁ ብትነግሩኝ፥ ሠላሳ የበፍታ ቀሚስና ሠላሳ ልውጥ ልብስ እሰጣችኋለሁ፤

13፤ መፍታትም ባትችሉ ሠላሳ የበፍታ ቀሚስና ሠላሳ ልውጥ ልብስ ትሰጡኛላችሁ አላቸው። እነርሱም። እንድንሰማው እንቆቅልሽህን ንገረን አሉት።

14፤ እርሱም። ከበላተኛው ውስጥ መብል ወጣ፥ ከብርቱም ውስጥ ጥፍጥ ወጣ አላቸው። ሦስት ቀንም እንቈቅልሹን መተርጎም አልቻሉም።

15፤ በአራተኛውም ቀን የሶምሶንን ሚስት። እንቈቅልሹን እንዲነግረን ባልሽን ሸንግዪው፥ አለዚያም እንቺንና የአባትሽን ቤት በእሳት እናቃጥላለን፤ ወደዚህ ጠራችሁን ልትገፉን ነውን? አሉአት።

16፤ የሶምሶንም ሚስት በፊቱ እያለቀሰች። በእውነት ጠልተኸኛል፥ ከቶም አትወድደኝም፤ ለሕዝቤ ልጆች እንቈቅልሽ ሰጥተሃቸዋልና ትርጓሜውንም አልነገርኸኝም አለችው። እርሱም። እነሆ፥ ለአባቴና ለእናቴ አልነገርኋቸውም፥ ለአንቺ እነግርሻለሁን? አላት።

17፤ ሰባቱንም የበዓል ቀን በፊቱ አለቀሰች፤ እርስዋም ነዝንዛዋለችና በሰባተኛው ቀን ነገራት። ትርጓሜውንም ለሕዝብዋ ልጆች ነገረች።

18፤ በሰባተኛውም ቀን ፀሐይ ሳትገባ የከተማይቱ ሰዎች። ከማር የሚጣፍጥ ምንድር ነው? ከአንበሳስ የሚበረታ ማን ነው? አሉት። እርሱም። በጥጃዬ ባላረሳችሁ የእንቈቅልሼን ትርጓሜ ባላወቃችሁ ነበር አላቸው።

19፤ የእግዚአብሔርም መንፈስ በላዩ በኃይል ወረደ፤ ወደ አስቀሎናም ወረደ፥ ከዚያም ሠላሳ ሰዎችን ገደለ፥ ልብሳቸውንም ወስዶ እንቈቅልሹን ለፈቱት ሰዎች ሰጠ። ቍጣውም ነደደ፥ ወደ አባቱም ቤት ወጣ።

20፤ የሶምሶን ሚስት ግን ከተባበሩት ከሚዜዎቹ ለአንደኛው ሆነች። a