ምዕራፍ 46።

1፤ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። በውስጠኛው አደባባይ ወደ ምሥራቅ የሚመለከተው በር ሥራ በሚሠራበት በስድስቱ ቀን ተዘግቶ ይቈይ፤ ነገር ግን በሰንበት ቀንና በመባቻ ቀን ይከፈት።

2፤ አለቃውም በስተ ውጭ ባለው በር በደጀ ሰላሙ መንገድ ገብቶ በበሩ መቃን አጠገብ ይቁም፥ ካህናቱም የእርሱን የሚቃጠለውን መሥዋዕትና የደኅንነቱን መሥዋዕት ያቅርቡ፥ እርሱም በበሩ መድረክ ላይ ይስገድ፤ ከዚያም በኋላ ይውጣ፥ በሩ ግን እስከ ማታ ድረስ አይዘጋ።

3፤ የአገሩም ሕዝብ በዚያ በር መግቢያ በእግዚአብሔር ፊት በሰንበታትና በመባቻ ይስገዱ።

4፤ አለቃውም በሰንበት ቀን ለእግዚአብሔር የሚያቀርበው የሚቃጠል መሥዋዕት ነውር የሌለባቸው ስድስት የበግ ጠቦቶች ነውርም የሌለበት አንድ አውራ በግ ይሁን፤

5፤ የእህሉም ቍርባን ለአውራ በጉ አንድ የኢፍ መስፈሪያ ይሁን፥ ለጠቦቶቹም የእህል ቍርባን እንደሚቻል ያህል ይሁን፥ ለአንዱም የኢፍ መስፈሪያ አንድ የኢን መስፈሪያ ዘይት ያቅርብ።

6፤ በመባቻም ቀን ነውር የሌለበትን አንድ ወይፈን፥ ነውር የሌለባቸውንም ስድስት ጠቦቶችና አንድ አውራ በግ ያቅርብ፤

7፤ ለወይፈኑም አንድ የኢፍ መስፈሪያ ለአውራውም በግ አንድ የኢፍ መስፈሪያ ለጠቦቶቹም እንደ ተቻለው ያህል፥ ለአንዱም የኢፍ መስፈሪያ አንድ የኢን መስፈሪያ ዘይት ለእህሉ ቍርባን ያቅርብ።

8፤ አለቃውም በሚገባበት ጊዜ በበሩ ደጀ ሰላም መንገድ ይግባ በዚያውም ይውጣ።

9፤ የአገሩ ሕዝብ ግን በየክብረ በዓሉ ቀን ወደ እግዚአብሔር ፊት በመጡ ጊዜ በሰሜን በር በኩል ሊሰግድ የሚገባው በደቡብ በር በኩል ይውጣ፥ በደቡብም በር የሚገባው በሰሜን በር በኩል ይውጣ፤ በፊት ለፊት ይውጣ እንጂ በገባበቱ በር አይመለስ።

10፤ በሚገቡበት ጊዜ አለቃው በመካከላቸው ይግባ በሚወጡበትም ጊዜ ይውጣ።

11፤ በበዓላትና በክብረ በዓል ቀኖች የእህሉ ቍርባን ለወይፈኑ አንድ የኢፍ መስፈሪያ፥ ለአውራ በጉ አንድ የኢፍ መስፈሪያ፥ ለጠቦቶቹም እንደሚቻለው ያህል፥ ለኢፍ መስፈሪያም አንድ የኢን መስፈሪያ ዘይት ይሆናል።

12፤ አለቃውም በፈቃዱ የሚያቀርበውን መሥዋዕት፥ የሚቃጠለውን መሥዋዕት፥ ወይም በፈቃዱ ለእግዚአብሔር የሚያቀርበውን የደኅንነቱን መሥዋዕት፥ ባቀረበ ጊዜ፥ ወደ ምሥራቅ የሚመለከተው በር ይከፈትለት፥ በሰንበትም ቀን እንደሚያደርግ የሚቃጠለውን መሥዋዕትና የደኅንነቱን መሥዋዕት ያቅርብ፤ ከዚያም በኋላ ይውጣ፥ ከወጣም በኋላ በሩ ይዘጋ።

13፤ በየዕለቱም ለሚቃጠል መሥዋዕት ነውር የሌለበትን የአንድ ዓመት በግ ጠቦት ለእግዚአብሔር ያቅርብ፤ በየማለዳው ያቅርበው።

14፤ ከእርሱም ጋር የእህልን ቍርባን፥ በኢን መስፈሪያ ሢሶ ዘይት የተለወሰ የኢፍ መስፈሪያ ስድስተኛ እጅ መልካም ዱቄትን፥ በየማለዳው ያቅርብ፤ ይህ በዘላለሙ ሥርዓት ለእግዚአብሔር የዘወትር የእህል ቍርባን ይሁን።

15፤ እንዲሁ ዘወትር ለሚቃጠለው መሥዋዕት ጠቦቱንና የእህሉን ቍርባን ዘይቱንም በየማለዳው ያቅርብ።

16፤ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። አለቃው ከልጆቹ ለአንዱ ከርስቱ ስጦታ ቢሰጥ ለልጆቹ ይሁን፤ የርስት ይዞታ ይሆንላቸዋል።

17፤ ነገር ግን ከባሪያዎቹ ለአንዱ ከርስቱ ስጦታ ቢሰጥ እስከ ነጻነት ዓመት ድረሰ ለእርሱ ይሁን፥ ከዚያም በኋላ ለአለቃው ይመለስ፤ ርስቱ ግን ለልጆቹ ይሁን።

18፤ አለቃውም ሕዝቡን ከይዞታቸው ያወጣቸው ዘንድ ከርስታቸው በግድ አይውሰድ፤ ሕዝቤ ሁሉ ከይዞታቸው እንዳይነቀሉ ከገዛ ይዞታው ለልጆች ርስትን ይስጥ።

19፤ በበሩም አጠገብ ባለው መግቢያ ወደ ሰሜን ወደሚመለከተው ለካህናት ወደሚሆን ወደ ተቀደሰው ዕቃ ቤት አገባኝ፤ እነሆም፥ በኋላው በምዕራብ በኩል አንድ ስፍራ ነበረ።

20፤ እርሱም። ካህናቱ ሕዝቡን ለመቀደስ ወደ ውጭው አደባባይ እንዳያወጡ የበደሉን መሥዋዕትና የኃጢአቱን መሥዋዕት የሚቀቅሉበት፥ የእህሉንም ቍርባን የሚጋግሩበት ስፍራ ይህ ነው አለኝ።

21፤ በውጭው አደባባይ አወጣኝ በአደባባይም ወዳለው ወደ አራቱ ማዕዘን አዞረኝ፤ እነሆም፥ በአደባባዩ ማዕዘን ሁሉ አደባባይ ነበረ።

22፤ በአደባባዩ በአራቱ ማዕዘን ርዝመቱ አርባ ክንድ ወርዱም ሠላሳ ክንድ የሆነ የታጠረ አደባባይ ነበረ፤ በማዕዘኑ ላሉ ለእነዚህ ለአራቱ ስፍራዎች አንድ ልክ ነበረ።

23፤ በአራቱም ዙሪያ ሁሉ ግንብ ነበረ፥ በግንቡም ሥር በዙሪያው የመቀቀያ ቦታ ነበረ።

24፤ እርሱም። እነዚህ የቤቱ አገልጋዮች የሕዝቡን መሥዋዕት የሚቀቅሉባቸው ስፍራዎች ናቸው አለኝ።