ምዕራፍ 20።

1፤ እግዚአብሔርም ይህን ቃል ሁሉ እንዲህ ብሎ ተናገረ።

2፤ ከግብፅ ምድር ከባርነት ቤት ያወጣሁህ እግዚአብሔር አምላክህ እኔ ነኝ።

3፤ ከእኔ በቀር ሌሎች አማልክት አይሁኑልህ።

4፤ በላይ በሰማይ ካለው፥ በታችም በምድር ካለው፥ ከምድርም በታች በውኃ ካለው ነገር የማናቸውንም ምሳሌ፥ የተቀረጸውንም ምስል ለአንተ አታድርግ።

5፤ አትስገድላቸው፥ አታምልካቸውምም፤ በሚጠሉኝ እስከ ሦስተኛና እስከ አራተኛ ትውልድ ድረስ የአባቶችን ኃጢአት በልጆች ላይ የማመጣ፤

6፤ ለሚወድዱኝ፥ ትእዛዜንም ለሚጠብቁ እስከ ሺህ ትውልድ ድረስ ምሕረትን የማደርግ እኔ እግዚአብሔር አምላክህ ቀናተኛ አምላክ ነኝና። ፕ

7፤ የእግዚአብሔርን የአምላክህን ስም በከንቱ አትጥራ፤ እግዚአብሔር ስሙን በከንቱ የሚጠራውን ከበደል አያነጻውምና።

8፤ የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ።

9፤ ስድስት ቀን ሥራ ተግባርህንም ሁሉ አድርግ፤

10፤ ሰባተኛው ቀን ግን ለእግዚአብሔር ለአምላክህ ሰንበት ነው፤ አንተ፥ ወንድ ልጅህም፥ ሴት ልጅህም፥ ሎሌህም፥ ገረድህም፥ ከብትህም፥ በደጆችህም ውስጥ ያለ እንግዳ በእርሱ ምንም ሥራ አትሥሩ፤

11፤ እግዚአብሔር በስድስት ቀን ሰማይንና ምድርን፥ ባሕርንም፥ ያለባቸውንም ሁሉ ፈጥሮ በሰባተኛው ቀን ዐርፎአልና፤ ስለዚህ እግዚአብሔር የሰንበትን ቀን ባርኮታል ቀድሶታልም።

12፤ አባትህንና እናትህን አክብር፤ እግዚአብሔር አምላክህ በሚሰጥህ ምድር ዕድሜህ እንዲረዝም።

13፤ አትግደል።

14፤ አታመንዝር።

15፤ አትስረቅ።

16፤ በባልንጀራህ ላይ በሐሰት አትመስክር።

17፤ የባልንጀራህን ቤት አትመኝ፤ የባልንጀራህን ሚስት ሎሌውንም ገረዱንም በሬውንም አህያውንም ከባልንጀራህ ገንዘብ ሁሉ ማናቸውንም አትመኝ።

18፤ ሕዝቡም ሁሉ ነጐድጓዱንና መብረቁን፥ የቀንደ መለከቱን ድምፅ፥ ተራራውንም ሲጤስ አዩ፤ ሕዝቡም ባዩ ጊዜ ተርበደበዱ፥ ርቀውም ቆሙ።

19፤ ሙሴንም። አንተ ተናገረን እኛም እንሰማለን፤ እንዳንሞት ግን እግዚአብሔር አይናገረን አሉት።

20፤ ሙሴም ለሕዝቡ። እግዚአብሔር ሊፈትናችሁ፥ ኃጢያትንም እንዳትሠሩ እርሱን መፍራት በልባችሁ ይሆን ዘንድ መጥቶአልና አትፍሩ አለ።

21፤ ሕዝቡም ርቀው ቆሙ፥ ሙሴም እግዚአብሔር ወዳለበት ወደ ጨለማው ቀረበ።

22፤ እግዚአብሔር ሙሴን አለው። ለእስራኤል ልጆች እንዲህ በል። እኔ ከሰማይ እንደ ተናገርኋችሁ እናንተ አይታችኋል።

23፤ በአጠገቤ ምንም አታድርጉ፤ የብር አማልክት የወርቅም አማልክት ለእናንተ አታድርጉ።

24፤ የጭቃ መሠዊያ ሥራልኝ፥ የሚቃጠለውንና የደኅንነት መሥዋዕትህን በጎችህንም በሬዎችህንም ሠዋበት፤ ስሜን በማሳስብበት ስፍራ ሁሉ ወደ አንተ መጥቼ እባርክሃለሁ።

25፤ የድንጋይም መሠዊያ ብታደርግልኝ ብረት በነካው ድንጋይ አትሥራው፤ በመሣሪያ ብትነካው ታረክሰዋለህና።

26፤ ኃፍረተ ሥጋህ በእርሱ እንዳይገለጥ ወደ መሠዊያዬ በደረጃ አትውጣ።