ምዕራፍ 17። ድፕ ች

17

1፤ አኪጦፌልም አቤሴሎምን። አሥራ ሁለት ሺህ ሰዎች ልምረጥና

1 አኪጦፌልም በዚህች ሌሊት ተነሥቼ ዳዊትን ላሳድድ።

2፤ ደክሞና እጁ ዝሎ ሳለ እወድቅበታለህ፥ አስፈራውማለሁ፤ ከእርሱም ጋር ያለው ሕዝብ ሁሉ ይሸሻል፥ ንጉሡንም ብቻውን እመታዋለሁ፤

3፤ ሙሽራ ወደ ባልዋ እንደምትመለስ ሕዝቡን ሁሉ ወደ አንተ እመልሰዋለሁ፤ ሕዝቡ ሁሉ ደኅና ይሆናል፤ የምትፈልገው አንድ ሰው ብቻ ነው።

4፤ ነገሩም አቤሴሎምንና የእስራኤልን ሽማግሌዎች ሁሉ ደስ አሰኘ።

5፤ አቤሴሎምም። አርካዊውን ኩሲን ጥሩ፥ ደግሞም እርሱ የሚለውን እንስማ አለ።

6፤ ኩሱም ወደ አቤሴሎም በመጣ ጊዜ አቤሴሎም። አኪጦፌል ያለው ይህ ነው፤ ነገሩን እናደርገው ዘንድ ይገባልን? ባይሆን ግን አንተ ንገረን ብሎ ተናገረው።

7፤ ኩሲም አቤሴሎምን። አኪጦፌል በዚህ ጊዜ የመከራት ምክር መልካም አይደለችም አለው።

8፤ ኩሲ ደግሞ አለ። ግልገሎችዋ በዱር በተነጠቁ ጊዜ ድብ መራራ እንደ ሆነች በልባቸው መራሮች እጅግም ኃያላን መሆናቸውን አባትህንና ሰዎቹን ታውቃለህ፤ አባትህ አርበኛ ነው፥ ከሕዝብም ጋር አያድርም።

9፤ አሁንም ምናልባት በአንድ ጕድጓድ ወይም በማናቸውም ስፍራ ተሸሽጎ ይሆናል፤ በመጀመሪያም ከእነርሱ አያሌዎች ቢወድቁ፥ የሚሰማው ሁሉ። አቤሴሎምን የተከተለው ሕዝብ ተመታ ይላል።

10፤ እስራኤልም ሁሉ አባትህ ኃያል እንደ ሆነ፥ ከእርሱም ጋር ያሉት ሰዎች ጽኑዓን እንደ ሆኑ ያውቃልና ጽኑዕ ልቡም እንደ አንበሳ ልብ የሆነው ፈጽሞ ይቀልጣል።

11፤ ነገር ግን የምመክርህ ይህ ነው፤ ከዳን እስከ ቤርሳቤህ ያለ እስራኤል ሁሉ በብዛቱ እንደ ባሕር አሸዋ ሆኖ ወደ አንተ ይሰብሰብ፥ አንተም በመካከላቸው ወደ ሰልፍ ውጣ።

12፤ እርሱንም ወደምናገኝበት ወደ አንድ ስፍራ እንደርስበታለን፥ ጠልም በምድር ላይ እንደሚወድቅ እንወርድበታለን፤ እርሱና ከእርሱም ጋር ያሉ ሰዎች ሁሉ አንድ ስንኳ አናስቀርም።

13፤ ወደ ከተማም ቢገባ እስራኤል ሁሉ ወደዚያች ከተማ ገመድ ይወስዳል፥ እኛም አንድ ድንጋይ እንኳ እስከማይገኝባት ድረስ ወደ ወንዙ ውስጥ እንስባታለን።

14፤ አቤሴሎምና የእስራኤልም ሰዎች ሁሉ። የአርካዊው የኩሲ ምክር ከአኪጦፌል ምክር ይሻላል አሉ። እግዚአብሔርም በአቤሴሎም ላይ ክፉ ያመጣ ዘንድ እግዚአብሔር መልካሚቱን የአኪጦፌልን ምክር እንዲበትን አዘዘ።

15፤ ኩሲም ለካህናቱ ለሳዶቅና ለአብያታር። አኪጦፌል ለአቤሴሎምና ለእስራኤል ሽማግሌዎች እንዲህና እንዲህ መክሮአል፤ እኔ ግን እንዲህና እንዲህ መክሬአለሁ።

16፤ አሁን እንግዲህ ንጉሡና ከእርሱ ጋር ያለው ሕዝብ ሁሉ እንዳይዋጡ፥ ፈጥናችሁ። ሳትዘገይ ተሻገር እንጂ በዚህች ሌሊት በምድረ በዳ መሻገሪያ አትደር ብላችሁ ለዳዊት ንገሩት አላቸው።

17፤ ዮናታንና አኪማአስ ተገልጠው ወደ ከተማ ይገቡ ዘንድ አልቻሉም ነበርና በዓይንሮጌል ተቀምጠው ነበር፤ አንዲትም ባሪያ ሄዳ ትነግራቸው ነበር፤ እነርሱም ሄደው ለንጉሡ ለዳዊት ይነግሩት ነበር።

18፤ አንድ ብላቴናም አይቶ ለአቤሴሎም ነገረው፤ እነርሱ ግን ፈጥነው ሄዱ፤ ወደ ብራቂምም ወደ አንድ ሰው ቤት መጡ፤ በግቢውም ውስጥ ጕድጓድ ነበረ፥ ወደዚያም ውስጥ ወረዱ።

19፤ ሴቲቱም በጕድጓድ አፍ ላይ ዳውጃ ዘረጋችበት፥ የተከካ እህልም በላዩ አሰጣችበት፤ ነገሩም እንዲህ ተሰወረ።

20፤ የአቤሴሎም ባሪያዎች ወደ ሴቲቱ ወደ ቤት መጥተው። አኪማአስና ዮናታን የት አሉ? አሉ፤ ሴቲቱም። ፈፋውን ተሻግረው ሄዱ አለቻቸው። እነርሱም ፈልገው ባላገኟቸው ጊዜ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ።

21፤ ከሄዱም በኋላ እነርሱ ከጕድጓድ ወጥተው ሄዱ፥ ለንጉሡም ለዳዊት ነገሩት፥ ዳዊትንም። አኪጦፌል በእናንተ ላይ እንዲህ መክሮአልና ተነሡ፥ ፈጥናችሁም ውኃውን ተሻገሩ አሉት።

22፤ ዳዊትና ከእርሱም ጋር የነበሩት ሁሉ ተነሥተው ዮርዳኖስን ተሻገሩ፤ እስኪነጋም ድረስ ዮርዳኖስን ሳይሻገር አንድ ሰው እንኳ አልቀረም።

23፤ አኪጦፌልም ምክሩን እንዳልተከተሉ ባየ ጊዜ አህያውን ጫነ፥ ተነሥቶም ወደ ቤቱ ወደ ከተማው ሄደ፤ ቤቱንም አደራጅቶ በገዛ እጁ ታንቆ ሞተ፥ በአባቱም መቃብር ተቀበረ።

24፤ ዳዊትም ወደ መሃናይም መጣ፤ አቤሴሎምም ከእርሱም ጋር የእስራኤል ሰዎች ሁሉ ዮርዳኖስን ተሻገሩ።

25፤ አቤሴሎምም በጭፍራው ላይ በኢዮአብ ስፍራ አሜሳይን ሾመ፤ አሜሳይም የይስማኤላዊ ሰው የዬቴር ልጅ ነበረ፤ እርሱም የኢዮአብን እናት የጽሩያን እኅት የናዖስን ልጅ አቢግያን አግብቶ ነበር።

26፤ እስራኤልና አቤሴሎምም በገለዓድ ምድር ሰፈሩ።

27፤ ዳዊትም ወደ መሃናይም በመጣ ጊዜ በአሞን ልጆች አገር በረባት የነበረ የናዖስ ልጅ ኡኤስቢ፥ የሎዶባርም ሰው የዓሚኤል ልጅ ማኪር፥ የሮግሊምም ሰው ገለዓዳዊ ቤርዜሊ፥

28፤29፤ ሕዝቡ በምድረ በዳ ተርቦአል፥ ደክሞአል፥ ተጠምቶአል ብለው ምንጣፍ፥ ዳካ፥ የሸክላም ዕቃ፥ ይበሉም ዘንድ ስንዴ፥ ገብስ፥ ዱቄት፥ የተጠበሰ እሸት፥ ባቄላ፥ ምስር፥ የተቈላ ሽንብራ፥ ማር፥ ቅቤ፥ በጎች፥ የላምም እርጎ ለዳዊትና ከእርሱ ጋር ለነበሩት ሕዝብ አመጡላቸው።