መዝሙር 52

ለመዘምራን አለቃ፤ ኤዶማዊው ዶይቅ መጥቶ ለሳኦል። ዳዊት ወደ አቢሜሌክ ቤት መጥቶአል ብሎ በነገረው ጊዜ፤ የዳዊት ትምህርት።

1 ኃያል ሆይ፥ በክፋት ለምን ትጓደዳለህ? ሁልጊዜስ በመተላለፍ?

2 አንደበትህ ኃጢአትን ያስባል፤ እንደ ተሳለ ምላጭ ሽንገላን አደረግህ።

3 ከመልካም ይልቅ ክፋትን፥ ጽድቅንም ከመናገር ይልቅ ዓመፃን ወደድህ።

4 የሚያጠፉ ቃልን ሁሉ፥ የሽንገላ ምላስን ወደድህ።

5 ስለዚህ እግዚአብሔር ለዘላለም ያፈርስሃል፤ ከቤትህም ይነቅልሃል ያፈልስሃልም፥ ሥርህንም ከሕያዋን ምድር።

6 ጻድቃን አይተው ይፈራሉ፤ በእርሱም ይሥቃሉ እንዲህም ይላሉ።

7 እግዚአብሔርን ረዳቱ ያላደረገ፥ በባለጠግነቱም ብዛት የታመነ፥ በከንቱ ነገርም የበረታ ያ ሰው እነሆ።

8 እኔስ በእግዚአብሔር ቤት እንደ ለመለመ እንደ ወይራ ዛፍ ነኝ፤ ለዓለምና ለዘላለም በእግዚአብሔር ምሕረት ታመንሁ።

9 አድርገህልኛልና ለዘላለም አመሰግንሃለሁ፥ በቅዱሳንህም ዘንድ መልካም ነውና ስምህን ተስፋ አደርጋለሁ።