መዝሙር 132

የመዓርግ መዝሙር።

1 አቤቱ፥ ዳዊትን ገርነቱንም ሁሉ አስብ፤

2 ለእግዚአብሔር እንደ ማለ፥ ለያዕቆብም አምላክ እንደ ተሳለ።

3 በእውነት ወደ ቤቴ ድንኳን አልገባም፥ ወደ ምንጣፌም አልጋ አልወጣም፥

4 ለዓይኖቼም መኝታ ለሽፋሽፍቶቼም እንቅልፍ፥ ለጕንጮቼም ዕረፍትን አልሰጥም፥

5 ለእግዚአብሔር ስፍራ፥ ለያዕቆብ አምላክ ማደሪያ እስካገኝ ድረስ ብሎ።

6 እነሆ፥ በኤፍራታ ሰማነው፥ በዱር ውስጥም አገኘነው።

7 ወደ ማደሪያዎቹ እንገባለን፤ እግሮቹ በሚቆሙበት ስፍራ እንሰግዳለን።

8 አቤቱ፥ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፥ አንተና የመቅደስህ ታቦት።

9 ካህናቶችህ ጽድቅን ይልበሱ፥ ቅዱሳንህም ደስ ይበላቸው።

10 ስለ ዳዊት ስለ ባሪያህ የቀባኸውን ሰው ፊት አትመልስ።

11 እግዚአብሔር ለዳዊት በእውነት ማለ አይጸጸትምም፥ እንዲህ ብሎ። ከሆድህ ፍሬ በዙፋንህ ላይ አስቀምጣለሁ።

12 ልጆችህ ኪዳኔን፥ ይህንም የማስተምራቸውን ምስክሬን ቢጠብቁ፥ ልጆቻቸው ደግሞ በዙፋንህ ላይ ለዘላለም ይቀመጣሉ።

13 እግዚአብሔር ጽዮንን መርጦአታልና፥ ማደሪያውም ትሆነው ዘንድ ወድዶአታልና፥ እንዲህ ብሎ።

14 ይህች ለዘላለም ማረፊያዬ ናት፤ መርጫታለሁና በዚህች አድራለሁ።

15 አሮጊቶችዋን እጅግ እባርካለሁ፥ ድሆችዋንም እንጀራ አጠግባለሁ።

16 ካህናቶችዋንም ደኅንነትን አለብሳቸዋለሁ፥ ቅዱሳኖችዋም እጅግ ደስ ይላቸዋል።

17 በዚያ ለዳዊት ቀንድን አበቅላለሁ፥ ለቀባሁትም ሰው መብራትን አዘጋጃለሁ።

18 ጠላቶችንም እፍረትን አለብሳቸዋለሁ፤ በእርሱ ግን ቅድስናዬ ያብባል።