መዝሙር 124

የዳዊት የመዓርግ መዝሙር።

1 እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ባይሆን እስራኤል እንዲህ ይበል።

2 እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ባይሆን ሰዎች በእኛ ላይ በተነሡ ጊዜ፥

3 ቍጣቸውን በላያችን በነደደ ጊዜ፥ በዚያን ጊዜ ሕያዋን ሳለን በዋጡን ነበር፤

4 በዚያን ጊዜ ውኃ ባሰጠመን ነበር፥ በነፍሳችንም ላይ ፈሳሽ ባለፈ ነበር፤

5 በዚያን ጊዜ የጐርፍ ውኃ በነፍሳችን ላይ ባለፈ ነበር።

6 ለጥርሳቸው ንክሻ ያላደረገን እግዚአብሔር ይባረክ።

7 ነፍሳችን እንደ ወፍ ከአዳኞች ወጥመድ አመለጠች። ወጥመድ ተሰበረ እኛም አመለጥን።

8 ረድኤታችን ሰማይንና ምድርን በሠራ በእግዚአብሔር ስም ነው።