መዝሙር 115

1 ለእኛ አይደለም፥ አቤቱ፥ ለእኛ አይደለም፥ ነገር ግን ለስምህ ስለ ምሕረትህ ስለ እውነትህም ምስጋናን ስጥ።

2 አሕዛብ። አምላካቸው ወዴት ነው? አይበሉ።

3 አምላካችንስ በላይ በሰማይ ነው፤ በሰማይም በምድርም የፈቀደውን ሁሉ አደረገ።

4 የአሕዛብ ጣዖታቶች የወርቅና የብር፥ የሰው እጅ ሥራ ናቸው።

5 አፍ አላቸው አይናገሩምም፤ ዓይን አላቸው አያዩምም፤

6 ጆሮ አላቸው አይሰሙምም፤ አፍንጫ አላቸው አያሸትቱምም፤

7 እጅ አላቸው አይዳሰሱምም፤ እግር አላቸው አይሄዱምም፤ በጕሮሮአቸውም አይናገሩም።

8 የሚሠሩአቸውም የሚያምኑባቸውም ሁሉ እንደ እነርሱ ይሁኑ።

9 የእስራኤል ቤት ሆይ፥ በእግዚአብሔር ታመኑ፤ ረድኤታቸውና መታመኛቸው እርሱ ነው።

10 የአሮን ቤት ሆይ፥ በእግዚአብሔር ታመኑ ረድኤታቸውና መታመኛቸው እርሱ ነው።

11 እግዚአብሔርን የምትፈሩ ሆይ፥ በእግዚአብሔር ታመኑ፤ ረድኤታቸውና መታመኛቸው እርሱ ነው።

12 እግዚአብሔር አሰበን ይባርከንማል፤ የእስራኤልን ቤት ይባረካል፥ የአሮንንም ቤት ይባረካል።

13 እግዚአብሔርን የሚፈሩትን፥ ትንንሾችንና ትልልቆችን ይባርካል።

14 እግዚአብሔር በላያችሁ፥ በላያችሁና በልጆቻችሁ ላይ ይጨምር።

15 እናንተ ሰማይንና ምድርን ለሠራ ለእግዚአብሔር የተባረካችሁ ናችሁ።

16 የሰማያት ሰማይ ለእግዚአብሔር ነው፤ ምድርን ግን ለሰው ልጆች ሰጣት።

17 አቤቱ፥ ሙታን የሚያመሰግኑህ አይደሉም ወደ ሲኦልም የሚወርዱ ሁሉ፤

18 እኛ ሕያዋን ግን ከዛሬ ጀምሮ እስከ ዘላለም እግዚአብሔርን እንባርካለን። ሃሌ ሉያ።