ምዕራፍ 23።

1፤ ኢዮብም መለሰ እንዲህም አለ።

2፤ ዛሬም ደግሞ የኅዘን እንጕርጕሮዬ ገና መራራ ነው፤

እጁ በልቅሶ ጩኸቴ ላይ ከብዳለች።

3፤ እርሱን ወዴት እንዳገኘው ምነው ባወቅሁ!

ወደ ተቀመጠበትስ ስፍራ ምነው በደረስሁ!

4፤ በፊቱ ሙግቴን አዘጋጅ ነበር፥

አፌንም በማስረጃ እሞላው ነበር።

5፤ የሚመልስልኝም ቃል ምን እንደ ሆነ አውቅ ነበር፥

የሚለኝንም አስተውል ነበር።

6፤ በኃይሉ ብዛት ከእኔ ጋር ይምዋገት ነበርን?

እንኳን! ያደምጠኝ ነበር።

7፤ ቅን ሰው ከእርሱ ጋር በዚያ ይከራከር ነበር፤

እኔም ከፈራጄ ለዘላለም እድን ነበር።

8፤ እነሆ፥ ወደ ፊት እሄዳለሁ፥ እርሱም የለም፤

ወደ ኋላም እሄዳለሁ፥ እኔም አላስተውለውም፤

9፤ ወደሚሠራበት ወደ ግራ ብሄድ አልመለከተውም፤

በቀኜም ይሰወራል፥ አላየውምም፤

10፤ የምሄድበትን መንገድ ያውቃል፤

ከፈተነኝም በኋላ እንደ ወርቅ እወጣለሁ።

11፤ እግሬ ወደ እርምጃው ተጣብቆአል፤

መንገዱንም ጠብቄአለሁ፥ ፈቀቅም አላልሁም።

12፤ ከከንፈሩ ትእዛዝ አልተመለስሁም፤

የአፉን ቃል በልቤ ሰውሬአለሁ።

13፤ እርሱ ግን ብቻውን ነው፤ እርሱንስ የሚመስለው ማን ነው?

ነፍሱም የወደደችውን ያደርጋል።

14፤ በእኔ ላይ የተወሰነውን ይፈጽማል፤

እንደዚህም ያለ ብዙ ነገር በእርሱ ዘንድ አለ።

15፤ ስለዚህ በፊቱ ደነገጥሁ፤

ባሰብሁም ጊዜ ከእርሱ ፈራሁ።

16፤ እግዚአብሔር ልቤን አባብቶታልና፥

ሁሉንም የሚችል አምላክ አስደንግጦኛል።

17፤ ከጨለማው የተነሣ፥

ድቅድቁም ጨለማ ፊቴን ከመክደኑ የተነሣ አልደነገጥሁም።