ምዕራፍ 12።

1፤ ኢዮብም መለሰ እንዲህም አለ።

2፤ በእርግጥ እናንተ ዓይነተኞች ሰዎች ናቸሁ፤

ጥበብም ከእናንተ ጋር ይሞታል።

3፤ ነገር ግን እኔ ደግሞ እንደ እናንተ ማስተዋል አለኝ፤

ከእናንተም የማንስ አይደለሁም፤

እንደዚህ ያለውን ነገር የማያውቅ ማን ነው?

4፤ እግዚአብሔርን የጠራሁ እርሱም የመለሰልኝ እኔ

ለባልንጀራው መሳለቂያ እንደሚሆን ሰው ሆኛለሁ፤

ጻድቅና ፍጹም ሰው መሳለቂያ ሆኖአል።

5፤ ተዘልሎ በሚቀመጥ ሰው አሳብ መከራ ይናቃል፤

ነገር ግን እግሩን ሊያድጠው ተዘጋጅቶአል።

6፤ የቀማኞች ድንኳን በደኅንነት ይኖራል፥

እግዚአብሔርንም የሚያስቈጡ ተዘልለው ተቀምጠዋል፤

እግዚአብሔር ሁሉን በእጃቸው አምጥቶላቸዋል።

7፤ አሁን ግን እንስሶችን ጠይቅ፥ ያስተምሩህማል፤

የሰማይንም ወፎች ጠይቅ፥ ይነግሩህማል።

8፤ ወይም ለምድር ተናገር፥ እርስዋም ታስተምርሃለች፤

የባሕርም ዓሣዎች ይነግሩሃል።

9፤ የእግዚአብሔር እጅ ይህን እንዳደረገ

ከእነዚህ ሁሉ የማያውቅ ማን ነው?

10፤ የሕያዋን ሁሉ ነፍስ

የሰውም ሁሉ መንፈስ በእጁ ናት።

11፤ ምላስ መብልን እንደሚቀምስ፥

ጆሮ ቃልን የሚለይ አይደለምን?

12፤ በሽምግልና ጊዜ ጥበብ፥

በዘመንስ ርዝመት ማስተዋል ይገኛል።

13፤ በእግዚአብሔር ዘንድ ጥበብና ኃይል አለ፤

ለእርሱ ምክርና ማስተዋል አለው።

14፤ እነሆ፥ ይፈርሳል፥ የፈረሰውም ተመልሶ አይሠራም፤

በሰውም ቢዘጋበት የሚከፍትለት የለም።

15፤ እነሆ፥ ውኆቹን ይከለክላል፥ እነርሱም ይደርቃሉ፤

እንደ ገና ይሰድዳቸዋል፥ ምድሪቱንም ይገለብጣሉ።

16፤ ኃይልና ጥበብ በእርሱ ዘንድ ናቸው፤

የሚስተውና የሚያስተው ለእርሱ ናቸው።

17፤ መካሮችንም እንደ ዘረፋ ይወስዳቸዋል፥

ፈራጆችንም ያሳብዳል።

18፤ የነገሥታትንም እስራት ይፈታል፥

ወገባቸውንም በመታጠቂያ ያስራቸዋል።

19፤ ካህናትን እንደ ዘረፋ ይወስዳቸዋል፥

ኃያላንንም ይገለብጣቸዋል።

20፤ ከታመኑ ሰዎችም ቋንቋን ያርቃል፥

የሽማግሌዎችንም ማስተዋል ይወስድባቸዋል።

21፤ በአለቆች ላይ ንቀትን ያፈስሳል፥

የብርቱዎችንም መታጠቂያ ያላላል።

22፤ ጥልቅ ነገር ከጨለማ ይገልጣል፥

የሞትንም ጥላ ወደ ብርሃን ያወጣል።

23፤ አሕዛብን ከፍ ከፍ ያደርጋል፥ እነርሱንም ያጠፋል፤

አሕዛብንም ያሰፋል፥ እነርሱንም ያፈልሳቸዋል።

24፤ ከምድር አሕዛብ አለቆች ዘንድ ማስተዋልን ይወስዳል፥

መንገድም በሌለበት በረሃ ያቅበዘብዛቸዋል።

25፤ ብርሃንም ሳይኖር በጨለማ ይርመሰመሳሉ፤

እንደ ሰካራም ይቅበዘበዛሉ።