ምዕራፍ 49

1 ስለ አሞን ልጆች፤ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። ለእስራኤል ልጆች የሉትምን? ወይስ ወራሽ የለውምን? ስለ ምን ሚልኮም ጋድን ወረሰ? ሕዝቡስ በከተሞቹ ላይ ስለ ምን ተቀመጠ?

2 ስለዚህ፥ እነሆ፥ በአሞን ልጆች ከተማ በረባት ላይ የሰልፍ ውካታን የማሰማበት ዘመን ይመጣል፥ ይላል እግዚአብሔር፤ የፍርስራሽ ክምርም ትሆናለች፥ ሴቶች ልጆችዋም በእሳት ይቃጠላሉ፥ እስራኤልም የወረሱትን ይወርሳል፥ ይላል እግዚአብሔር።

3 ሐሴቦን ሆይ፥ ጋይ ፈርሳለችና አልቅሺላት እናንተም የረባት ሴቶች ልጆች ሆይ፥ ሚልኮም ካህናቱና አለቆቹም በአንድነት ይማረካሉና ጩኹ፥ ማቅም ታጠቁ፥ አልቅሱም፥ በቅጥሮችም መካከል ተርዋርዋጡ።

4 ማን ይመጣብኛል ብለሽ በመዝገብሽ የታመንሽ አንቺ ከዳተኛ ልጅ ሆይ፥ በሸለቆችሽ፥ ውኃ በሚያረካቸው ሸለቆችሽ፥ ስለ ምን ትመኪያለሽ?

5 እነሆ፥ በዙሪያሽ ካሉት ሁሉ ዘንድ ፍርሃትን አመጣብሻለሁ፥ ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፤ እያንዳንዳችሁም በፊታችሁ ወዳለው ስፍራ ትሰደዳላችሁ፥ የሚሸሹትንም የሚሰበስብ የለም።

6 ነገር ግን ከዚያ በኋላ የአሞንን ልጆች ምርኮ እመልሳለሁ፥ ይላል እግዚአብሔር።

7 ስለ ኤዶምያስ፤ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። በውኑ በቴማን ጥበብ የለምን? ከብልሃተኞችስ ምክር ጠፍቶአልን?

8 ጥበባቸውስ አልቆአልን? እናንተ በድዳን የምትኖሩ ሆይ፥ የዔሳውን ጥፋት፥ የምጐበኝበትን ጊዜ፥ አመጣበታለሁና ሽሹ፥ ወደ ኋላ ተመለሱ፥ በጥልቅም ውስጥ ተቀመጡ።

9 ወይን ለቃሚዎች ቢመጡብህ፥ ቃርሚያውን አይተውልህምን? ሌቦችስ በሌሊት ቢመጡ፥ የሚያጠፉት እስኪበቃቸው ድረስ አይደለምን?

10 እኔ ግን ዔሳውን ዐራቈትሁት፥ የተሸሸጉትንም ስፍራዎች ገለጥሁ፥ ይሸሸግም ዘንድ አይችልም፤ ዘሩም ወንድሞቹም ጎረቤቶቹም ጠፍተዋል እርሱም የለም።

11 ድሀ አደጎችህን ተው፥ እኔም በሕይወት አኖራቸዋለሁ፤ መበለቶችህም በእኔ ይታመኑ።

12 እግዚአብሔር እንዲህ ይላልና። እነሆ፥ ጽዋውን ያልተገባቸው ሰዎች ጠጥተውታል፤ አንተም ሳትቀጣ ትቀራለህን? በእርግጥ ትጠጣለህ እንጂ ያለ ቅጣት አትቀርም።

13 ባሶራ መደነቂያና መሰደቢያ መረገሚያም እንድትሆን በራሴ ምያለሁ፥ ይላል እግዚአብሔር፤ ከተሞችዋም ሁሉ ለዘላለም ባድማ ይሆናሉ።

14 ከእግዚአብሔር ዘንድ ወሬ ሰምቻለሁ በአሕዛብም መካከል። ተሰብሰቡ፥ በእርስዋም ላይ ኑ ለሰልፍም ተነሡ የሚል መልእክተኛ ተልኮአል።

15 እነሆ፥ በአሕዛብ ዘንድ የተጠቃህ፥ በሰዎችም ዘንድ የተናቅህ አድርጌሃለሁ።

16 በዓለት ንቃቃት ውስጥ የምትቀመጥ፥ የተራራውን ከፍታ የምትይዝ ሆይ፥ ድፍረትህና የልብህ ኵራት አታልለውሃል። ቤትህን ምንም እንደ ንስር ከፍ ብታደርግ፥ ከዚያ አወርድሃለሁ፥ ይላል እግዚአብሔር።

17 ኤዶምያስም መደነቂያ ትሆናለች፥ የሚያልፍባትም ሁሉ ይደነቃል፥ ስለ መጣባትም መቅሠፍት ሁሉ ያፍዋጭባታል።

18 ሰዶምና ገሞራ በእነርሱም አጠገብ የነበሩት ከተሞች እንደ ተገለበጡ፥ ይላል እግዚአብሔር፥ እንዲሁ በዚያ ሰው አይቀመጥም የሰው ልጅም አይኖርባትም።

19 እነሆ፥ ከእርስዋ ዘንድ በቶሎ አባርራቸዋለሁና በጠነከረው አምባ ላይ ከዮርዳኖስ ትዕቢት ውስጥ እንደ አንበሳ ይወጣል፤ የተመረጠውንም በእርስዋ ላይ እሾመዋለሁ፤ እንደ እኔ ያለ ማን ነው? ወይስ ለእኔ ጊዜ የሚወስን ማን ነው? ወይስ ፊቴን የሚቃወም እረኛ ማን ነው?

20 ስለዚህ እግዚአብሔር በኤዶምያስ ላይ የመከረባትን ምክር፥ በቴማንም በሚኖሩ ሰዎች ላይ ያሰባትን አሳብ ስሙ፤ በእውነት የመንጋ ትንንሾች ይጐተታሉ፤ በእውነት ማደሪያቸውን ባድማ ያደርግባቸዋል።

21 ከመውደቃቸው ድምፅ የተነሣ ምድር ተናወጠች፥ የጩኸታቸውም ድምፅ በኤርትራ ባሕር ተሰማ።

22 እነሆ፥ እንደ ንስር ወጥቶ ይበራል ክንፉንም በባሶራ ላይ ይዘረጋል፥ በዚያም ቀን የኤዶምያስ ኃያላን ልብ ምጥ እንደ ያዛት ሴት ልብ ይሆናል።

23 ስለ ደማስቆ፤ ክፉ ወሬ ሰምተዋልና ሐማትና አርፋድ አፈሩ ቀለጡም፤ በባሕርም ላይ ኅዘን አለ፥ ታርፍም ዘንድ አትችልም።

24 ደማስቆ ደከመች ትሸሽም ዘንድ ዘወር አለች እንቅጥቅጥም ያዛት፥ እንደ ወላድም ሴት ጣርና ምጥ ያዛት።

25 የተመሰገነችው ከተማ፥ የደስታዬ ከተማ፥ ሳትለቀቅ እንዴት ቀረች?

26 ስለዚህ ጐበዛዝትዋ በአደባባይዋ ላይ ይወድቃሉ፥ በዚያም ቀን ሰልፈኞች ሁሉ ይጠፋሉ፥ ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር።

27 በደማስቆም ቅጥር ላይ እሳት አነድዳለሁ የወልደ አዴርንም አዳራሾች ትበላለች።

28 የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነፆር ስለ መታ ስለ ቄዳርና ስለ አሶር መንግሥታት፤ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። ተነሡ ወደ ቄዳርም ውጡ፥ የምሥራቅንም ልጆች አጥፉ።

29 ድንኳናቸውንና መንጋቸውን ይወስዳሉ፤ መጋረጆቻቸውንና ዕቃቸውን ሁሉ ግመሎቻቸውንም ለራሳቸው ይወስዳሉ፥ በዙሪያቸውም ሁሉ ጥፋትን ጥሩባቸው።

30 እናንተ በአሶር የምትኖሩ ሆይ፥ የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነፆር ተማክሮባችኋልና፥ አሳብም አስቦባችኋልና ሽሹ ወደ ሩቅም ሂዱ በጥልቅም ውስጥ ተቀመጡ፥ ይላል እግዚአብሔር።

31 ተነሡ፥ ዕርፊት ወዳለበት ተዘልሎም ወደ ተቀመጠው፥ ደጅና መወርወሪያ ወደሌለው ብቻውንም ወደ ተቀመጠው ሕዝብ ውጡ።

32 ግመሎቻቸው ይበዘበዛሉ የእንስሶቻቸውም ብዛት ይማረካል፤ ጠgWraቸውንም በዙሪያ የሚላጩትን ሰዎች ወደ ነፋሳት ሁሉ እበትናቸዋለሁ፤ ከዳርቻቸውም ሁሉ ጥፋት አመጣባቸዋለሁ፥ ይላል እግዚአብሔር።

33 አሶርም የቀበሮ መኖሪያና የዘላለም ባድማ ትሆናለች፤ በዚያም ሰው አይኖርም፥ የሰው ልጅም አይቀመጥባትም።

34 በይሁዳ ንጉሥ በሴዴቅያስ መንግሥት መጀመሪያ ስለ ኤላም ወደ ነቢዩ ወደ ኤርምያስ የመጣው የእግዚአብሔር ቃል ይህ ነው።

35 የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። እነሆ፥ዋና የኃይላቸው መሣሪያ የሆነውን የኤላምን ቀስት እሰብራለሁ።

36 ከአራቱም ከሰማይ ማዕዘናት አራቱን ነፋሳት በኤላም ላይ አመጣለሁ፥ ወደ እነዚያም ነፋሳት ሁሉ እበትናቸዋለሁ፤ ከኤላም የተሰደዱ ሰዎች የማይደርሱበት ሕዝብ አይገኝም።

37 በጠላቶቻቸውና ነፍሳቸውን በሚሹአት ፊት ኤላምን አስደነግጣለሁ፤ ክፉ ነገርን እርሱም ጽኑ ቍጣዬን አመጣባቸዋለሁ፥ ይላል እግዚአብሔር፤ እስካጠፋቸውም ድረስ በኋላቸው ሰይፍ እሰድድባቸዋለሁ፤

38 ዙፋኔንም በኤላም አኖራለሁ ከዚያም ንጉሡንና አለቆቹን አጠፋለሁ፥ ይላል እግዚአብሔር።

39 ነገር ግን በኋለኛው ዘመን የኤላምን ምርኮ እመልሳለሁ፥ ይላል እግዚአብሔር።