ምዕራፍ 10።

1፤ እኔም አየሁ፥ እነሆም፥ በኪሩቤል ራስ ላይ ባለው ጠፈር በላያቸው እንደ ሰንፔር ድንጋይ ያለ እንደ ዙፋን የሚመስል መልክ ተገለጠ።

2፤ በፍታም የለበሰውን ሰው። በመንኰራኵሮች መካከል ከኪሩብ በታች ግባ፥ ከኪሩቤልም መካከል ካለው እሳት ፍም እጆችህን ሙላ በከተማይቱም ላይ በትናት ብሎ ተናገረው። እኔም እያየሁ ገባ።

3፤ ሰውዬውም ሲገባ ኪሩቤል በቤቱ ቀኝ በኩል ቆመው ነበር፥ ደመናውም ውስጠኛውን አደባባይ ሞላ።

4፤ የእግዚአብሔር ክብርም ከኪሩቤል ወጥቶ በቤቱ መድረክ ላይ ቆመ፤ ቤቱም በደመናው ተሞላ፥ አደባባዩም በእግዚአብሔር ክብር ፀዳል ተሞላ።

5፤ ሁሉንም የሚችል አምላክ እንደሚናገረው ያለ ጽምፅ እንዲሁ የኪሩቤል ክንፎች ድምፅ እስከ ውጭው አደባባይ ድረስ ተሰማ።

6፤ በፍታም የለበሰውን ሰው። ከመንኰራኵሮች ከኪሩቤል መካከል እሳት ውሰድ ብሎ ባዘዘው ጊዜ እርሱ ገብቶ በአንድ መንኰራኵር አጠገብ ቆመ።

7፤ ኪሩብም ከኪሩቤል መካከል እጁን በኪሩቤል መካከል ወዳለው እሳት ዘርግቶ ከዚያ ወሰደ፥ በፍታም በለበሰው ሰው እጅ አኖረው፤ እርሱም ይዞ ወጣ።

8፤ በኪሩቤልም ከክንፎቻቸው በታች የሰው እጅን መሳይ ታየ።

9፤ እኔም አየሁ፥ እነሆም፥ በኪሩቤል አጠገብ አራት መንኰራኵሮች ነበሩ፤ አንዱ መንኰራኵር በአንዱ ኪሩብ፥ አንዱ መንኰራኵር በአንዱ ኪሩብ አጠገብ ነበረ። የመንኰራኵሮቹም መልክ እንደ ቢረሌ ድንጋይ ነበረ።

10 የአራቱም መልክ አንድ ይመስል ነበር፥ መልካቸውም በመንኰራኵር ውስጥ እንዳለ መንኰራኵር ነበረ።

11፤ ሲሄዱም በአራቱ ጐድናቸው ይሄዱ ነበር፥ ሲሄዱም አይገላመጡም ነበር፥ ራሱ ወደምታመለክትበት ስፍራ ወደዚያ ይከተሉ ነበር፤ ሲሄዱም አይገላመጡም ነበር።

12፤ ገላቸውም ሁሉ ጀርባቸውም እጃቸውም ክንፋቸውም መንኰራኵሮቹም፥ ለአራቱ የነበሩ መንኰራኵሮች፥ በዙሪያቸው ዓይኖች ተሞልተው ነበር።

13፤ መንኰራኵሮችም እኔ እየሰማሁ ጌልጌል ተብለው ተጠሩ።

14፤ ለእያንዳንዱም አራት አራት ፊት ነበሩት፤ አንደኛው ፊት የኪሩብ ፊት፥ ሁለተኛውም የሰው ፊት፥ ሦስተኛው የአንበሳ ፊት፥ አራተኛውም የንስር ፊት ነበረ።

15፤ ኪሩቤልም ከፍ ከፍ አሉ፤ ይህ በኮቦር ወንዝ ያየሁት እንስሳ ነው።

16፤ ኪሩቤልም ሲሄዱ መንኰራኵሮቹ በአጠገባቸው ይሄዱ ነበር፤ ኪሩቤልም ከምድር ከፍ ከፍ ይሉ ዘንድ ክንፎቻቸውን ሲዘረጉ መንኰራኵሮች ደግሞ ከአጠገባቸው ፈቀቅ አይሉም ነበር።

17፤ ሕይወት ያላቸው የእንስሶች መንፈስ በመንኰራኵሮች ውስጥ ነበረና እነዚህ ሲቆሙ እነዚያ ይቆሙ ነበር፥ እነዚህም ከፍ ከፍ ሲሉ እነዚያ ከእነርሱ ጋር ከፍ ከፍ ይሉ ነበር።

18፤ የእግዚአብሔርም ክብር ከቤቱ መድረክ ላይ ወጥቶ በኪሩቤል ላይ ቆመ።

19፤ ኪሩቤልም ክንፎቻቸውን ዘረጉ እኔም እያየሁ ከምድር ከፍ ከፍ አሉ፤ በወጡም ጊዜ መንኰራኵሮች በአጠገባቸው ነበሩ፤ በእግዚአብሔርም ቤት በምሥራቁ በር መግቢያ ቆሙ፥ የእስራኤልም አምላክ ክብር በላያቸው ላይ ነበረ።

20፤ ይህ በኮበር ወንዝ ከእስራኤል አምላክ በታች ያየሁት እንስሳ ነው፥ ኪሩቤልም እንደ ነበሩ አስተዋልሁ።

21፤ ለእያንዳንዱ አራት አራት ፊት፥ ለእያንዳንዱም አራት አራት ክንፍ ነበሩት፥ የሰውም እጅ አምሳያ ከክንፎቻቸው በታች ነበረ።

22፤ ፊቶቻቸውም በኮቦር ወንዝ ያየኋቸውን ፊቶች ይመስሉ ነበር፤ እነርሱና መልካቸውም እንዲሁ ነበረ፤ እያንዳንዱም አቅንቶ ወደ ፊት ይሄድ ነበር።