ምዕራፍ 6።

1፤ የነቢያትም ልጆች ኤልሳዕን። እነሆ፥ በፊትህ የምንቀመጥበት ስፍራ ጠብቦናል።

2፤ ወደ ዮርዳኖስም እንሂድ፥ ከእኛም እያንዳንዱ ከዚያ ምሰሶ ያምጣ፥ የምንቀመጥበትንም ስፍራ በዚያ እንሥራ አሉት፤ እርሱም። ሂዱ አለ።

3፤ ከእነርሱም አንዱ። አንተ ደግሞ ከእኛ ከባሪያዎችህ ጋር ለመሄድ ፍቀድ አለ። እርሱም። እሄዳለሁ አለ።

4፤ ከእነርሱም ጋር ሄደ፤ ወደ ዮርዳኖስም በደረሱ ጊዜ እንጨት ቆረጡ።

5፤ ከእነርሱም አንዱ ምሰሶውን ሲቆርጥ የምሳሩ ብረት ወደ ውኃው ውስጥ ወደቀ፤ እርሱም። ጌታዬ ሆይ፥ ወየው! ወየው! የተዋስሁት ነበረ ብሎ ጮኽ።

6፤ የእግዚአብሔርም ሰው። የወደቀው ወዴት ነው? አለ ስፍራውንም አሳየው፤ እንጨትም ቆርጦ በዚያ ጣለው፥ ብረቱም ተንሳፈፈ።

7፤ እርሱም። ውሰደው አለ፤ እጁንም ዘርግቶ ወሰደው።

8፤ የሶርያም ንጉሥ ከእስራኤል ጋር ይዋጋ ነበር፤ ከባሪያዎቹም ጋር ተማክሮ። በዚህ ተደብቀን እንሰፍራለን አለ።

9፤ የእግዚአብሔርም ሰው። ሶርያውያን በዚያ ተደብቀዋልና በዚያ ስፍራ እንዳታልፍ ተጠንቀቅ ብሎ ወደ እስራኤል ንጉሥ ላከ።

10፤ የእስራኤልም ንጉሥ የእግዚአብሔር ሰው ወደ ነገረው ስፍራ ሰደደ፤ አንድ ጊዜም ሳይሆን፥ ሁለት ጊዜም ሳይሆን በዚያ ራሱን አዳነ።

11፤ የሶርያም ንጉሥ ልብ ስለዚህ እጅግ ታወከ፤ ባሪያዎቹንም ጠርቶ። ከእኛ ዘንድ ከእስራኤል ንጉሥ ጋር የተወዳጀ እንዳለ አትነግሩኝምን? አላቸው።

12፤ ከባሪያዎቹም አንዱ። ጌታዬ ሆይ፥ እንዲህ እኮ አይደለም፤ ነገር ግን በእልፍኝህ ውስጥ ሆነህ የምትናገረውን በእስራኤል ዘንድ ያለ ነቢይ ኤልሳዕ ለእስራኤል ንጉሥ ይነግረዋል አለ።

13፤ እርሱም። ልኬ አስይዘው ዘንድ ሄዳችሁ ወዴት እንደ ሆነ እዩ አለ። እነርሱም። እነሆ፥ በዶታይን አለ ብለው ነገሩት።

14፤ ወደዚያም ፈረሶችንና ሰረገሎችን እጅግም ጭፍራ ሰደደ፤ በሌሊትም መጥተው ከተማይቱን ከበቡ።

15፤ የእግዚአብሔር ሰው ሎሌ ማለዳ ተነሥቶ በወጣ ጊዜ፥ እነሆ፥ በከተማይቱ ዙሪያ ጭፍራና ፈረሶች ሰረገሎችም ነበሩ። ሎሌውም። ጌታዬ ሆይ፥ ወዮ! ምን እናደርጋለን? አለው።

16፤ እርሱም። ከእኛ ጋር ያሉት ከእነርሱ ጋር ካሉት ይበልጣሉና አትፍራ አለው።

17፤ ኤልሳዕም። አቤቱ፥ ያይ ዘንድ ዓይኖቹን፥ እባክህ፥ ግለጥ ብሎ ጸለየ። እግዚአብሔርም የብላቴናውን ዓይኖች ገለጠ፥ አየም፤ እነሆም፥ በኤልሳዕ ዙሪያ ያሉት የእሳት ፈረሶችና ሰረገሎች ተራራውን ሞልተውት ነበር።

18፤ ወደ እርሱም በወረዱ ጊዜ ኤልሳዕ። ይህን ሕዝብ ዕውር ታደርገው ዘንድ እለምንሃለሁ ብሎ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ። ኤልሳዕም እንደ ተናገረው ቃል ዕውር አደረጋቸው።

19፤ ኤልሳዕም። መንገዱ በዚህ አይደለም፥ ከተማይቱም ይህች አይደለችም፤ የምትሹትን ሰው አሳያችሁ ዘንድ ተከተሉኝ አላቸው፤ ወደ ሰማርያም መራቸው።

20፤ ወደ ሰማርያም በገቡ ጊዜ ኤልሳዕ። አቤቱ፥ ያዩ ዘንድ የእነዚህን ሰዎች ዓይኖች ግለጥ አለ፤ እግዚአብሔርም ዓይኖቻቸውን ገለጠ፥ እነርሱም አዩ። እነሆም፥ በሰማርያ መካከል ነበሩ።

21፤ የእስራኤልም ንጉሥ ባያቸው ጊዜ አልሳዕን። አባቴ ሆይ፥ ልግደላቸውን? ልግደላቸውን? አለው።

22፤ እርሱም። አትግደላቸው፤ በሰይፍህና በቀስትህ የማረክኸውን ትገድል ዘንድ ይገባሃልን? እንጀራና ውኃ በፊታቸው አኑርላቸው፥ በልተውና ጠጥተውም ወደ ጌታቸው ይሂዱ አለው።

23፤ ብዙም መብል አዘጋጀላቸው፤ በበሉና በጠጡ ጊዜም አሰናበታቸው፥ እነርሱም ወደ ጌታቸው ሄዱ። ከዚያም በኋላ የሶርያ አደጋ ጣዮች ወደ እስራኤል አገር አልመጡም።

24፤ ከዚያም በኋላ የሶርያ ንጉሥ ወልደ አዴር ሠራዊቱን ሁሉ ሰበሰበ፥ ወጥቶም ሰማርያን ከበባት።

25፤ በሰማርያም ታላቅ ራብ ሆኖ ነበር፤ እነሆም፥ የአህያ ራስ በአምሳ ብር፥ የርግብም ኩስ የጎሞር ስምንተኛ የሚሆን በአምስት ብር እስኪሸጥ ድረስ ከበቡአት።

26፤ የእስራኤልም ንጉሥ በቅጥር ላይ በተመላለሰ ጊዜ አንዲት ሴት ጌታዬ ንጉሥ ሆይ፥ እርዳኝ ብላ ወደ እርሱ ጮኸች።

27፤ እርሱም። እግዚአብሔር ያልረዳሽን እኔ እንዴት እረዳሻለሁ? ከአውድማው ወይስ ከመጥመቂያው ነውን? አለ።

28፤ ንጉሡም። ምን ሆነሻል? አላት፤ እርስዋም። ይህች ሴት። ዛሬ እንድንበላው ልጅሽን አምጪ፤ ነገም ልጄን እንበላለን አለችኝ።

29፤ ልጄንም ቀቅለን በላነው፤ በማግሥቱም። እንድንበላው ልጅሽን አምጪ አልኋት፤ ልጅዋንም ሸሸገችው ብላ መለሰችለት።

30፤ ንጉሡም የሴቲቱን ቃል ሰምቶ ልብሱን ቀደደ፤ በቅጥርም ይመላለስ ነበር፤ ሕዝቡም በስተ ውስጥ በሥጋው ላይ ለብሶት የነበረውን ማቅ አዩ።

31፤ ንጉሡም። የሣፋጥ ልጅ የኤልሳዕ ራስ ዛሬ በላዩ ያደረ እንደ ሆነ እግዚአብሔር ይህን ያድርግብኝ፥ ይህንም ይጨምርብኝ አለ።

32፤ ኤልሳዕ ግን በቤቱ ተቀምጦ ነበር፥ ሽማግሌዎችም ከእርሱ ጋር ተቀምጠው ነበር፤ ንጉሡ ሰው ላካ፤ መልእክተኛውም ገና ሳይደርስ ለሽማግሌዎች። ይህ የነፍሰ ገዳይ ልጅ ራሴን ይቈርጥ ዘንድ እንደ ላከ እዩ፤ መልእከተኛውም በመጣ ጊዜ ደጁን ዘግታችሁ ከልክሉት፤ የጌታው የእግሩ ኮቴ በኋላው ነው አላቸው።

33፤ ሲናገራቸውም መልእክተኛው ወደ እርሱ ደረሰ፤ እርሱም። እነሆ፥ ይህ ክፉ ነገር ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው፥ እግዚአብሔርን ገና እጠብቅ ዘንድ ምንድር ነኝ? አለ።